Wednesday, March 4, 2015

ድምፃዊ ጃኪ ጎሲ ከብርሃኑ ተዘራ ጋር ወገኔ እያለ በሰራው ዘፈን የተነሳ አዲስ አበባ ከደህንነት ሃይሎች ማስፈራሪያ እየደረሰው መሆኑ ተሰማ ::

ጃኪ እና ብርሃኑ ከሙዚቃ አቀናባሪው ሄኖክ ነጋሽ ጋር በስቱዲዮ ውስጥ
ጃኪ የተቀረጸው ዘፈኑን በሄኖክ ነጋሽ ኮምፒውተር ሲያደምጥ

(ዘ-ሐበሻ) ብርሃኑ ተዘራ (ብሬ ላላ) ከጃኪ ጎሲ ጋር የሠራው ወቅታዊ ዘፈን በብዙዎች ዘንድ ተወዳጅነትን ካተረፈ በኋላ አዲስ አበባ የሚገኘው ድምፃዊ ጃኪ ጎሲ ስልኩ በደህንነቶች መጠለፉን እና በስር ዓቱ ሰዎችም ከፍተኛ ማስፈራሪያና ዛቻ እየደረሰው እንደሚገኝ ለድምጻዊው ቅርብ የሆኑ ወገኖች ለዘ-ሐበሻ አስታወቁ::

በዛሬው ዕለት ድምፃዊ ጃኪ ጎሲ ፃፈው በሚል “ዘፈኑን ተሰርቄ ነው; ጃኪ የፖለቲካ ዘፈን አይዘፍንም” የሚል ጽሁፍ በፌስቡክ የተሰራጨ ሲሆን ይህ ጽሁፍ በአድናቂዎቹ እንጂ በጃኪ ጎሲ አለመፃፉን የደረሰን መረጃ ያመለክታል:: የጃኪ ጎሲ የግል 2 ፌስቡክ አካውንቶቹ ላይ ይህ ዜና እስከተዘገበበት ጊዜ ድረስ ከብርሃኑ ተዘራ ጋር ስለዘፈነው ዘፈን የሰጠው አስተያየት የለም:: ሆኖም የድምጻዊው አድናቂዎች ዘፈኑ ካለርሱ እውቅና ውጭ የተሰራ አድርገው የለጠፉት መረጃ ብዙዎችን ከማደናገሩም በላይ በተለይ ለአራት ቀናት ጃኪ ጎሲ በዋሽንግተን ዲሲ የሙዚቃ አቀናባሪው ሄኖክ ነጋሽ ጋር ሄዶ ከብርሃኑ ጋር ሲቀረጽ የተመለከቱ የዓይን እማኞች “ጃኪ ለምን ይዋሻል?” የሚሉ አስተያየቶችን በየሶሻል ሚዲያው እያሰራጩ ነው:: ድምፃዊ ጃኪ ጎሲ በፌስቡክ ገጹ ምንም ያለው ነገር ባለመኖሩ አስተያየት ከመስጠት መቆጠብ ይሻላል የሚሉ ወገኖች; ጃኪ በስሙ በወጣ መግለጫ የተነሳ በስሙና በቀጣይ ሥራው ላይ ከፍተኛ ኪሳራ ሳያደርስበት አቋሙን እንዲያሳውቅ ጠይቀዋል::


ጃኪ በአሁኑ ወቅት አዲስ አበባ የሚገኝ ሲሆን የደህንነት ኃይሎች ስልኩን በመጥለፍ ከማን ጋር እንደሚያወራ እንደሚከታተሉት ዘፈኑን እንዲያስተባብል ከፍተኛ ጫና እያደረጉበት መሆኑን ለድምፃዊው ቅርብ የሆኑ ምንጮች ጠቁመዋል:: ጃኪ ከዚ ቀደም “ማን እንደ ሃገር” የሚል ነጠላ ዘፈን ሰርቶ የለቀቀ ሰሞን ዋሽንግተን ዲሲ የሚገኘው የድምፅአዊው የቅርብ ወዳጅ ተወዛዋዡ አብዮት መሃል ላይ ሰማያዊ የሌለበትን አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ባንዲራ በኪሊፕ ሰርቶ ሲለቅ ጃኪም ይህን የሙዚቃ ክሊፕ ፌስቡኩ ላይ ሼር ሲያደርግ ደህንነቶች እንዴት ሕገመንግስቱ የማይፈቅደውን ባንዲራ በክሊፑ ላይ ትጠቀማለህ? በሚል ባደረሱበት ማስፈራሪያ ከፌስቡክ ገጹ ዘፈኑን ማስወጣቱን የሚጠቅሱት እነዚሁ የቅርብ ወገኖች አሁንም ደህንነቶች በሚያደርሱበት ወከባ ከፍተኛ ጫና ውስጥ እንደሚገኝ ጠቁመዋል::


http://www.zehabesha.com/amharic/archives/39518



No comments:

Post a Comment