Thursday, August 14, 2014

ወያኔ በተቃዋሚ ፓርቲዎች ላይ የሚያደርሰው ቅጥ ያጣ አፈናና በደል

'

አሁን በስልጣን የሚገኘው የወያኔው ስርአት ላለፉት 22 አመታት የዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ እያለ ጆሮአችንን ቢያደነቁረውም እሱ የሚለው የዲሞክራሲ ስርዓትና ትክክለኛው ዲሞክራሲያዊ ስርአት አራምባና ቆቦ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን ዲሞክራሲያዊ ስርአትን በገመድ ለክቶና መጥኖ የናንተ መብትና ነጻነት እስከመጨፈር እንጂ የኔን ስልጣንና ጥቅም የሚነካ ከሆነ ቢላ ባንገቴ ካለን ሰነባበተ:: ለዚህም ይመስላል በተለይም ህገ መንግስታዊ መብታቸውን ተጠቅመው የተቃውሞ ድምጻቸውን ለሚያሰሙ ጋዜጠኞችም ሆነ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ምንም አይነት መፈናፈኛ እንዳያገኙ ሌት ተቀን ደፋ ቀና የሚለው::

ከዚህም የነጻነት እጦት እና ፍጹም አምባገነናዊ አፈናዎች መካከል እንደ አንድ ማሳያ የሚሆነው በተቃዋሚ ፓርቲዎች ላይ የሚያደርሰው ቅጥ ያጣ አፈናና በደል ሲሆን ዛሬ በወያኔው ስርዓት ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚታዩት እንደ ተፎካካሪ ፓርቲ ሳይሆን ሃገርን ለማፍረስ እንደተዘጋጁ አሸባሪዎች ተደርገው ነው:: በጣም የሚያሳዝነውነና አደገኛው አካሄዱ ደግሞ ይህን እምነቱን ቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲያምንና እንዲቀበል ፍጹም ህገወጥ በሆነና ከዕውነት በራቀ ውንጀላ ተቃዋሚዎችን ለማጠልሸት የሚያደርገው እልህ አስጨራሽ ትግሉ ነው::

ስርዓቱ በተለይም ከ1997 ዓ.ም ወዲህ ተቃዋሚዎችን ለማዳከምና ለማጥፋት ፍጹም ኢ-ፍትሃዊና ህገወጥ በሆነ መልኩ የሚያደርገው እንቅስቃሴ በሁለት ስትራቴጂዎች የተዋቀረ ነው::
የመጀመሪያውና ቀጥተኛው ስትራቴጂ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን አሸባሪና እሱ ራሱ አሸባሪ ናቸው ብሎ ከፈረጃቸው ድርጅቶች ጋር ማያያዝ (ማዛመድ) ነው:: ይህንንም ለማሳካት የተቃዋሚ ድርጅት አባሎችን ከአሸባሪ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት አላችሁ በሚል የፈጠራ ክስ መወንጀል ሲሆን በጣም በሚያሳፍርና በሚያሳዝን መልኩ በዚህ ስትራቴጂ ውስጥ ይቃወሙኛል ብሎ ያሰባቸውን የነጻው ሚዲያ ጋዜጠኞችንም ይጨምራል:: እንግዲህ ይህ ስትራቴጂ የተወሰኑ ግለሰቦችን በአሸባሪነት ክስ ወደ ዘብጥያ በማውረድ ብቻ የተገታ ወይም የተቋጨ ነው ብሎ የሚያስብ የዋህ ይኖራል ብዬ አላስብም ዋናው አላማ አማራጭ ሚዲያና እውነተኛ መረጃ የተነፈገው ቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ በፍርሃት ውስጥ እንዲሸማቀቅና ለትክክለኛ የዲሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ የሚኖረውን የጋለ የህዝብ ስሜት ጥቁር ጥላ እንዲያጠላበት የሚያደርግ እንጂ::

በዚህ ስትራቴጂ የኢትዮጵያ ህዝብ የወያኔውን ስርአት የሃሰት ውንጀላ ጠንቅቆ የሚያውቅ ቢሆንም ውሸት ሲደጋገም እውነት ይመስላል እንዲሉ አንድ ለናቱ በሆነው የገዢው ስርአት ሚዲያ በየቀኑ የሚቀርበው የሃሰት ፕሮፓጋንዳ ህዝቡ ለተቃዋሚዎች፣ ለገዢው ፓርቲም ይሁን ለጠቅላላ የፓለቲካው ድባብ የሚኖረው ስሜት በፍራቻ፣ በጥርጣሬና ቀላል በማይባል ሁኔታ በፓለቲካው ተስፋ የመቁረጥ ስሜት ውስጥ እንዲገባ የማድረግ ሃይሉ እጅግ ከፍተኛ ነው::

ከዚህም በተጨማሪ ይህንን አደገኛ አካሄድ የከፋ የሚያደርገው ደግሞ ተቃዋሚዎች ምንም አይነት ሃሳባቸውን የሚገልጹበት ነጻ ሚዲያ ሰለሌላቸው (ፍኖተ ነጻነት ጋዜጣ እንኳን እንደታፈነች ነች)በፈጠራ ክስ ለታሰሩ አባሎቻቸውም ሆነ ለደረሰባቸው የመልካም ገጽታ (Good Will) መበላሸት ማስተባበያ የመስጠትም ሆነ የመከላከል አቅሙ የሌላቸው መሆኑ ነው::
ሁለተኛውና ቀጥተኛ ያልሆነው ስትራቴጂ ከመጀመሪያው ስትራቴጂ ጋር የሚያያዝ ሲሆን ተቃዋሚዎች የመሰብሰብ፣ የመደራጀት ከህዝቡና ከደጋፊዎቻቸው ጋር የመገናኘትና የመቀስቀስ ስራዎቻቸውን እንዳይሰሩ በእጃዙርም ይሁን ባስ ሲልም በቀጥታ የማፈንና የማሰናከል ተግባር ነው::

ይህንን እቅዱን እውን ለማድረግም ተቃዋሚዎች የመሰብሰቢያ አዳራሾችን እንዳያገኙ የተለያዩ መሰናክሎችን መፍጠር፣ ራሳቸውን በገቢም ይሁን በተለያዩ ነገሮች ለማጠናከር የሚደረጉ ዝግጅቶችን ማስቆም፣ ማሰናከል፣ ተቃዋሚዎች የሚጠሩትን ሰላማዊ ሰልፎች አለመፍቀድ ወይም መሰረዝ፣ ምንም አይነት ነጻ ሚዲያ እንዳያገኙ መዝጋትና ሌሎችንም ዘዴዎች ይጠቀማል:፡

ሌላውን ሁሉ ትተን ዛሬ በጣም በሚሳዝን ሁኔታ በሃገራችን ለተቃዋሚዎች አንዱ ከባዱ ስራ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ማግኘት ነው:: ከተወሰኑ ጊዚያቶች በፊት ሰማያዊ ፓርቲ የመመስረቻ ጠቅላላ ጉባኤውን የሚያደርግበት አዳራሽ አጥቶ ምን ያህል እንደተቸገረ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው::ዛሬ ለአንድ ህጻን ልጅ ልደት ለማክበር እንኳን አዳራሽ በሽ በሆነበት ሃገር ተቃዋሚዎች መሰብሰቢያ አዳራሽ አጥተው በሰው ቤት ጓሮ ዳስ እየጣሉ ግማሹ ተሰብሳቢ ጸሃይ እየበላው ነው ስብሰባቸውን የሚያካሂዱት:: የሆቴል ቤት ባለቤቶችና አዳራሽ አከራዮች በወያኔው ስርዓት በሚደርስባቸው ከባድ ተጸዕኖ ለተቃዋሚዎች አዳራሾቻቸውን ለማከራየት ፈቃደኞች አይደሉም::

የሃገሪቷ ሃብት በወያኔዎች እጅ በወደቀበት በዚህ ሰዓት ኣንድ የሆቴል ቤት ባለቤት አዳራሹን ለተቃዋሚዎች ቢያከራይ በህብረተሰቡ ውስጥ በዘሩት የተቃዋሚዎችን ስም በሀሰት የማጠልሸት ተግባር፣ ፍራቻና የስጋት ድባብ እንዲሁም ወያኔዎችና ደጋፊዎቻቸው በሆቴሉ ላይ በሚጀምሩት የሃሰት አሉባልታ ሆቴሉ ቀስ በቀስ ከገበያ ውጭ ሊሆን ስለሚችልና ምናልባትም ካስፈለገ ሆቴሉን እስከማሳሸግ ሊደርሱ እንደሚችሉ ስለሚታወቅ ነው ( በ1997 ዓ.ም ምርጫ ወቅት የመርካቶው ምዕራብ ሆቴልና ሌሎችም ሆቴሎች ተቃዋሚዎችን ትረዳላቹ ተብለው ታሽገው እንደነበር አይዘነጋም::)


እንግዲህ ኢትዮጵያ ውስጥ በተቃውሞው ጎራ መሰለፍ እንደ ሃገር ጠላት የሚታይበት ደረጃ ላይ መድረስ ብቻ ሳይሆን ባስ ካለም አሸባሪ የሚል ታርጋ አስለጥፎ ወህኒ ሊያስወረውር የሚያስችልበት ሁኔታ ኢትዮጵያውያኖችን በነጻነት የሚፈልጉትን ደግፈው ወይም ተቃውመው መኖር እንዳይችሉ ብቻ ሳይሆን በፍርሃት እንዲሸማቀቁና እንዲሰጉ ምክንያት ሆኗል:: ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ የወያኔን ስርዓት መቃወም ስትጀምር በዚያውም ወደ እስር ቤት መቃረብህን ትረዳለህ:: አንተን ለመክሰስ የማስረጃ ጉዳይ ብዙም አያስጨንቅም በኢ- ማይልህ ላይ አንዳንድ መረጃዎችን ወይም ሞባይልህ ላይ ጥቂት መልእክቶችን መላክ (SMS) ማድረግ አንተን ዘብጥያ ለማውረድ በቂ ናቸው:: ( ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ ከወንድሙ ጋር በኢ-ሜይል ስለአባታቸው የህክምና ኦፕሬሽን (Operation) የተጻጻፉትን ኦፕሬሽን የሚለው ቃል ሌላ አላማ ተብሎ እንደማስረጃ የቀረበበት ሁኔታን ልብ ይሏል::)

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/33549

No comments:

Post a Comment