Wednesday, November 5, 2014

በአንድ አካባቢ ኢትዮጵያዊያን ላይ የሚካሄድ ጥቃት በሁሉም ኢትዮጵያዊ ላይ የሚካሄድ ጥቃት ነው! •

ጥቅምት 25፣2007 (ኖቨምበር 4፣2014)

ህወሓት/ኢህአዴግ በተለያዩ ኢትዮጵያውያን ላይ ያነጣጠረ የግፍ ተግባር ማካሄድና የከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲውን ተግባራዊ ማድረጉን በሰፊው ቀጥሏል::  በዚህ አኳያበሶማሌ፣ በአማራው፣ በኦሮሞ፣ በሲዳማ፣ በአፋር፣….ወዘተ ተወላጆች ላይ የሚያካሂደው እልቂት በቂ መረጃ ነው::
የዚህ ቀጣይ ረገጣ ተከታታይ ዒላማ የሆነው አንዱ የአማራው፡ተወላጅ ነው:: ህወሓት/ኢህአዴግ ከመነሻው የአማራ፡ተወላጁን  በጠላትነት ፈርጆ በተለያየ ደረጃየጥቃት ዒላማ አድርጎታል። በዚህም መሠረት በራሱ ትዕዛዝም ሆነ በተለጣፊ ድርጅቶቹ አማካኝነት እጅግ ዘግናኝ ግፍ የተሞላበት ወንጀል ፈጽሟል። ለዘመናት  ከኖረበት ቦታ “ወደ መጣህበት ሂድ” ተብሎ ንብረቱ ተነጥቆ ባዶ እጁን በግዳጅ እንዲባረር ተደርጓል። ይህ አልበቃ ብሎ ህፃናት ልጆች ሳይቀሩ አሰቃቂ በሆነ ግፍ እንዲታረዱ ዜጎች ወደ ገደል እንዲወረወሩና፣ ቤታቸው ውስጥ እንዳሉ እንዲቃጠሉ ተደርጓል። በአርባ ጉጉ፣ በወተር ፣በአርሲ .ወዘተ የተካሄደው ይህንኑ ነው የሚያሳየው።

ለዚህ ጨካኝና ህገወጥ ተግባርም የህወሓት/ኢህአዴግ ባለሥልጣኖች በቀጥታም በተዛዋሪም ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል። በጊዜው ጠቅላይ ሚኒስተር የነበረው ታምራት ላይኔ በአማራው ተወላጅ ላይ የኦጋዴን ህዝብ እርምጃ እንዲወስድ ያካሄደው ግልጽ የሆነ መገፋፋት፣ በአርሲ በተካሄደ እልቂት እነ ኩማ ደመቅሳ ዋና ተዋናን እንደነበሩ፣ መለሰ ዜናዊ ከጉራፈርዳ የተባረሩትንና ለአቤቱታ የመጡን ዜጎች እንኳን አባረሯችሁ የሚል አንድምታ  የሚሰጥ መግለጫ በይፋ መስጠቱ ጥቂቶቹ ማስረጃዎች ናቸው።
ይህ ህወሓት/ኢህአዴግ ሆን ብሎ የሚፈጽመውና የሚያበረታታው ህዝብን እርስ በርስ የማጫረስ ተግባር እጅግ እየሰፋ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተጠናከር በአደገኛፍጥነትመም በመቀጠል ላይ ነው።

ትላንት ከትላንት በስቲያ በተለያዩ ቦታዎች እንደተደረገው ሁሉ፣ ባለፉት ጥቂት ሳምንታትም ባለማቋረጥ በጋምቤላ አካባቢ በተመሳሳይ ሁኔታ በዋናነት በዚሁ በአማራ ተወላጆች ላይ ያነጣጠረ የድብደባ፣ የግድያና የማፈናቀል እርምጃ በሰፊው ተካሂዶ በመዠንገር አካባቢ ብቻ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሲሞቱ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ቆስለዋል፣ በሽዎች የሚቆጠሩ ደግሞ ተፈናቅለዋል።

ይህ ሁሉ ሲሆን፣ የዜጎችን ደህንነት የመጠበቅ ግዴታ ያለበት መንግሥት መንበር ላይ የተቀመጠው ህወሓት/ኢህአዴግ ሁኔታው እንዳይከሰት ቀድሞ ለመከላከልም ሆነ በጊዜ ለማስቆም የወሰደው ምንም እርምጃ የለም። ችግሩ ከተፈጠረ በኋላም ቢሆን የተጎዱትን ለመንከባከብ፣ ህክምና የሚሹትን ለመርዳት፣ መልሶ ለማቋቋምና ወንጀለኞቹን ለህግ ለማቅረብ የሚያደርገው ይህ ነው የሚባል ሙከራ አይታይም።  ይሀ ሁሉ  የሚያመለክተው ያለው ስርዓት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የዚህ ወንጀል አካል እንደሆነ ነው።
ሸንጎው የኢትዮጵያን ህዝብ አንዱን ከአንዱ በማጋጨት ሥልጣኑን ለማራዘም ህወሓት/ኢህአዴግ የሚያካሂደውን ቀጣይ ሀላፊነት የጎደለው ኢ-ሰብአዊ ግፍ አጥብቆ ያወግዛል። በአማራውም ሆነ በሌሎች ኢትዮጵያውያን ላይ በተከታታይ እየተካሄደ ያለውን የማፈናቀል፣የግድያ፣ የጅምላ እሰራትና  ሌሎች  ወንጀሎች ባስቸኳይ እንዲቆም ያሳስባል። እስካሁን የተፈጸመው ግፍ ሁሉ ብቃት ባለው እና  ከሥርዓቱ ባለሟሎች ነፃ በሆነ አካል እንዲጣራ፤ ወንጀለኞቹም ለፍርድ እንዲቀርቡ ያስገነዝባል።

በኦጋዴን፣ በኦሮሚያ፣ በሲዳማ፣ በአፋር፣ በወልቃይት እንዲሁም በሌሎች የሀገራችን ቦታዎች ውስጥ ይህ  ሥርዓት የሚያካሂደውን ማለቂያ የሌለው ግፍ ሸንጎ አጥብቆ ያወግዛል።

ሰዎችን በትውልዳቸው የተነሳ በጅምላ የጥቃት ሰላባ ማድረግ በዓለምአቀፍ ህግም አስጠያቂ እንደሆነ የዚህ ጥፋት ፈጻሚም አስፈጻሚም የሆኑ ሁሉ እንዲገነዘቡት በድጋሚ ለማሳሰብ እንወዳለን።

የዚህን  የግፍ ሥርዓት መጨረሻ ለማፋጠን ሁሉም ኢትዮጵያዊ አንድነቱን አጠናክሮ እንዲነሳ እናሳስባለን፡  በአንድ አካባቢ ኢትዮጳያዊያን ላይ  የሚካሄድ ጥቃት በሁሉም ኢትዮጵያዊ ላይ የሚካሄድ ጥቃት ነው!

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!


 http://www.zehabesha.com/amharic/archives/35951

No comments:

Post a Comment