Sunday, July 31, 2016

በጎንደር፣ በማክሰኝት፣ በምዕራብ በለሳና በበምዕራብ እስቴ ታላላቅ ሰልፎች ተደርገዋል | 4 አጫጭር መረጃዎች

ከሙሉቀን ተስፋው

1. በጎንደር ከተማ ከአምስት መቶ እስከ ስምንት መቶ ሺህ የሚቆጠር ሕዝብ ሰልፉን ማድመቁ የታወቀ ሲሆን ታሪካዊው ባህታዊ አባ አምሃ ኢየሱስ ሰላማዊ ሰልፉን በሚገባ መርተውታል፡፡ አባ አምሃ ኢየሱስ ለሃይማኖታቸውና ለአገራቸው ሟች እና ዓለምን በቃኝ ያሉ ባሕታዊ ናቸው፡፡ በርካታ ዓመታትን ሕወሓት አስሮ አሰቃይቷቸው ከእስር የተፈቱት በቅርብ ጊዜ ነው፡፡ አዘዞ ላይ ፖሊስ የተወሰኑ ወጣቶችን አስሮ ከሕዝቡ ጋር ግጭት ለመፍጠር ሞክሮ ነበር፡፡ ሆኖም ጀግናው የዐማራ ሕዝብ በአንድነት የታሰሩትን ወጣቶች አስፈትቶ በሰላም ወደ ቤቱ ገብቷል፡፡
አቶ ዘመነ ምሕረት በአቶ ማሙሸት አማረ የሚመራው መኢአድ ምክትል ፕሬዝዳንት ከማክሰኝት እስከ ጎንደር በእግራቸው 40 ኪሎ ሜትር ያክል ከተጓዙ በኋላ ጎንደር እንዳይገቡ ተከልክለዋል፡፡
ከደብረ ታቦር ከዐሥር በላይ የህዝብ ማመላለሻ አውቶቡስ ለሰልፉ የሚሔዱ ሰዎችን አገልግሎት ሰጥቷል፡፡

2. ምዕራብ በለሳ አርባያ፡- ትናንት ምሽት በግጥም የወልቃይት ጠገዴን ዐማራነት እንዲሁም የወያኔ መንግሥት በዐማራ ሕዝብ ላይ የሚያደርሰውን በደል በተመለከተ ሲዘፍን ያመሸን ጎልማሳ ፖሊስ አስሮት አደረ፡፡ ዛሬ ከአርባያ፣ ደንቀዝ፣ ጎሃላና አካባቢው የተሰባሰበው የበለሳ ዐማራ የታሠረውን ጎልማሳ አስፈትቶ በሰላማዊ ሰለፍ ወያኔንና የትግራይን ተስፋፊነት ሲያወግዝ ውሏል፡፡ ከእኩለ ቀን በኋላ ሰልፉ ተበትኗል፡፡ ከአምሳ ሺህ በላይ ሰው ተሳትፎበታል፡፡

3. ጎንደር ዙሪያ ማክሰኝት፣ ከጎንደር 40 ኪሎ ሜትር በምትገኘው የማክሰኝት ከተማ ዛሬ ከሰዓት በኋላ ወጣቶች ለሰልፍ ወጥተው ነበር፡፡ ወያኔ ሌባ ነው፤ ዐማራ አሸባሪ አይደለም የሚሉ መፈክሮች አሰምተዋል፡፡ የፖሊስ አባላት ሰልፉን ለመበተን ጥረት አድርገው ነበር፤ ሆኖም ወጣቶች የሚፈለገውን መልእክተ አሰምተው መርሀ ግብራቸውን በሚገባ መልኩ አጠናቀዋል፡፡


4. ምዕራብ እስቴ፣ መካነየሱስ፡ ከጉና ተራራ ሥር የደንሳ አምባን ተንተርሳ የከተመችው የመካነ ኢየሱስ ከተማ ዛሬ ከእኩለ ቀን ጀምሮ በሰላማዊ ሰልፍ እየተናጠች ትገኛለች፡፡ እንደ መረጃ አቀባዮቻችን ሰልፉ ከሰዓት በኋላ በአካባቢው ያለው ገበሬ ሁሉ እንደተቀላቀለው ለማወቅ ተችሏል፡፡

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/63629

No comments:

Post a Comment