Sunday, July 12, 2015

የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላይ እስሩ ቀጥሏል

በአዲስ አበባና በየክፍለ ሀገሩ የሚገኙ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላይ እስሩ ቀጥሏል፡፡ ትናንትናው ዕለት በሸዋ ሮቢት የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪዎች የሆኑት አቶ ዘነበ ደሳለኝ፣ አቶ መንግስቱ ተበጀ፣ አቶ ቴዎድሮስ ሀብቴ እንዲሁም አዲስ አበባ ውስጥ አቶ ደብሬ አሸናፊ ታድነው የታሰሩ ሲሆን በዛሬው ዕለት አቶ መርከቡ ሀይሌና አናኒያ ኢሳያስ ለእስር ተዳርገዋል፡፡

መርከቡ ሀይሌና አናኒያ ኢሳያስ ዛሬ ሀምሌ 4/2007 ዓ.ም ከጠዋቱ 4 ሰዓት ላይ አራት ኪሎ አካባቢ በፖሊስና ደህንነቶች ተይዘው ታስረዋል፡፡ እነ መርከቡ በተያዙበት ወቅት ፖሊስና ደህንነቶች ‹‹ብጥብጥ ልታስነሱ እየጣራችሁ መሆኑን ደርሰንበታል›› እንዳሉዋቸው ተገልጾአል፡፡ በተጨማሪም የሰማያዊ ፓርቲ አባል የሆነው ስለሽ ደቻሳ ሀምሌ 1/2007 ዓ.ም ከቤቱ በደህንነትና በፖሊስ ታፍኖ ከፍተኛ ድብደባ ከተፈፀመበት በኋላ ታስሯል፡፡ ስለሽ ደቻሳ በተፈፀመበት ድብደባም እጅና እግሩ ላይ ስብራት እንደደረሰበት ታውቋል፡፡ በተጨማሪም የሰማያዊ ፓርቲ ታዛቢ የነበረው አስፋው ጀማል በትናንትናው ዕለት በፖሊስ ተይዞ መታሰሩን ምንጮች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ መርከቡ ኃይሌና አናኒያ ኢሳያስ በአራዳ ፖሊስ መምሪያ እንዲሁም ስለሽ ደቻሳ 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ እንደታሰሩ ታውቋል፡፡


በተመሳሳይ እስሩ በየ ክፍለ ሀገሩን የቀጠለ ሲሆን በከፋ ዞን ጨላ ወረዳ 8 የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ‹‹ማዳበሪያ አልወስድም ብለዋል›› በሚል ለእስር እንደተዳረጉ ከቦታው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ ሌሎች የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በማዳበሪያ ሰበብ ድብደባ እየደረሰባቸው እንደሆነ የገለጹት የዞኑ የፓርቲው አስተባባሪዎች ነሲብ አደነ የተባለ የሰማያዊ ፓርቲ አባል ከፍተኛ ድብደባ ደርሶበት ሆስፒታል ውስጥ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

http://satenaw.com/amharic/archives/8587

No comments:

Post a Comment