Saturday, May 11, 2013


በሙስና ወንጀል በተጠረጠሩ ግለሰቦች ቤት ከፍተኛ ንብረትና ሰነዶች ተገኙ

የፌዴራል ፖሊስ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር በዋሉ ግለሰቦች መኖሪያ ቤት የፍርድ ቤት ማዘዣ በማውጣት ዛሬ ግንቦት 02/ 2005 ብርበራ አካሂዷል፡፡
ታዛቢዎችና ራሳቸው ተጠርጣሪዎች በተገኙበት በዚህ ብርበራ ከፍተኛ የገንዘብ መጠን፤ በርካታ የቤት ካርታዎች፤ የኤሌክትሮኒክ መሳሪያዎችና ሌሎች ከወንጀሉ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን  ሰነዶች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ፖሊስ ገልጧል፡፡
ከተጠርጣሪዎች መካከል በፌዴራል ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተር አቶ ገብረዋህድ ገብረጊዮርጊስ መኖሪያ ቤት ዉስጥ 200ሺ የኢትዮጵያ ብር፤ በኢትዮጵያ ብር ምንዛሬ 700ሺ የሚጠጋ 26ሺ ዩሮ፤ ፓዉንድና ሀገራቸው የማይታወቁ የገንዘብ ኖቶች፤ በለገዳዲና ለገጣፎ የሚገኙ የቦታ ካርታና ፕላን እንዲሁም የተለያዩ ሰነዶች መገኘታቸውን ፖሊስ አስታዉቋል፡፡
ፖሊስ ለኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት እንደገለፀው በፌዴራል ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን የጉምሩክ ስነ ስርዓት አፈፃፀም የስራ ሂደት፤ የኤርፖርት ጉምሩክ ድህረ ክሊራንስ ኦዲት የስራ ሂደትና የኤርፖርት ጉምሩክ ስነ ስርዓት የስራ ሂደት ቡድን መሪ በመሆን በተለያዩ ወቅቶች ካገለገሉ በኋላ ሚያዚያ 2004 ስራ በለቀቁት ሌላው ተጠርጣሪ አቶ አስመላሽ ወልደማርያም ቤት ደግሞ 1ሚሊዮን 947ሺ 675 ብር በጥሬ ገንዘብ ተገኝቷል፡፡
ተጠርጣሪዎችን ለህግ ለማቅረብ በፌዴራል የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽንና በብሄራዊ የመረጃና ደህንነት አገልግሎት የተካሄደው ጥምር ዘመቻ በእቅድ የተመራ፤ ህጋዊ ስርዓትን መሰረት ያደረገና የተሳካ እንደነበር የፌዴራል ፖሊስ ለኢሬቴድ ገልጧል፡፡
በሂደቱም ከወንጀሉ ጋር ቀጥተኛ ተያያዥነት ያላቸው መረጃዎች እየተሰባሰቡ መሆናቸውን በፌዴራል ፖሊስ የፋይናንስ ወንጀሎች ቡድን መሪ ኢንስፔክተር በለጠ ባለሚ  ተናግረዋል፡፡
በቀጣይም ፖሊስ በምርመራው ሂደት የደረሰበትን መረጃ ለህዝብ እንደሚያቀርብና ህብረተሰቡም ህግን ለማስከበርና ሙስናን ለመዋጋት መንግስት በሚያደርገው ጥረት ተሳትፎውን አጠናክሮ እንዲቀጥል የፌዴራል ፖሊስ ጥሪ አቅርቧል፡፡
ሪፖርተር፤ አብዲ ከማል
     Posted By.Dawit Demelash

No comments:

Post a Comment