Wednesday, May 22, 2013

በደቡብ ክልል የደረጃ እድገት በኢህአዴግ አባልነት ብቻ እንደሚሰጥ ተጋለጠ

may.22.2013 am




በደቡብ ክልል ደራሼ ወረዳ ትምህርት ጽህፈት ቤት የደረጃ ዕድገትም ሆነ ሱፐርቫይዘርነት በሙያ ብቃት ሳይሆን በኢህአዴግ አባልነት መሆኑን የፍኖተ ነፃነት ምንጮች አጋለጡ፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ የወረዳው ትምህርት ጽህፈት ቤት ለሱፐርቫይዘርነት ምደባ በሙያ ብቃት ሳይሆን በኢህአዴግ አባልነት ብቻ እንደሆነ የጠቆሙና እራሳቸውን ከኢህአዴግ አባልነት ያገለሉ ባለሙያዎች ከደረጃና ከደመወዝ ዝቅ እንዲደረጉ በደብዳቤ የተገለፀላቸው እንዳሉ ማረጋገጥ ተችሏል፡፡
የወረዳው ትምህርት ጽህፈት ቤት የመምህራን ፣ የርዕሳነ መምህራንና ሱፐርቫይዘሮች አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ ንጋቱ በበኩላቸው “ማንም ሰው የደረጃ ዕድገትም ሆነ ሱፐርቫይዘርነት በውድድር እንጂ በኢህአዴግ አባልነት የሚል መመሪያም ሆነ የሲቭል ሰርቪስ ህግ የለም፤ አሁን ተፈፅሟል የምትለኝ ከሆነ ስህተተት ነው” ሲሉ ምላሽ የሰጡ ሲሆን በወረዳው እንዲህ ዓይነት ችግር ከተፈጠረም ቅሬታውን በማቅረብ መፍትሄ እንደሚያገኝ ጠቁመዋል፡፡
ውጤት ተኮር አሞላልን በተመለከተ ቅሬታ ከቀረበባቸው ርዕሳነ መመህራን መካከል በወረዳው የጋሉ ሙሉ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር አቶ ላገሩ አበበ ወ/አረጋይ “እኔ ውጤት ተኮር ያልሞላሁለት መምህር የለም፣ በስራ ላይ የቀረም ሆነ ቀረ ያልኩት መምህር የለም” ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ በተለይ እኚሁ ርዕሰ መምህር የፖለቲካ አስተሳሰብ ልዩነት ያላቸውን መምህራን ፀረ-ልማት፣ ፀረ- ህገመንግስት በማለትና በማስፈራራት በስራ የተገኙ ሰራተኞችን በስራ ገበታቸው ላይ አልተገኙም በሚል ጫና እንደሚፈጥሩ ምንጮቻችን ገልፀዋል፡፡
የክልሉ የሰገን ህዝቦች ዞን መምህራን ማኀበር ሰብሳቢ መምህር ስንታየሁ ገ/ፃዲቅ በተለይ የመምህራኑ ቅሬታ ሲቀርብ እስካሁን ትብብር አለማድረጋቸው ተጠቁሟል፡፡
በጉዳዩ ዙሪያ የጠየቅናቸው የዞኑ ኢመማ ሰብሳቢ መምህር ስንታየሁ ገ/ፃዲቅ በተለይ ከደራሼ ወረዳ መምህራን ቅሬታ ይዘው የቀረቡት ሁለት ብቻ ሲሆኑ እነሱም መፍትሄ እንዳገኙ በመግለፅ መምህር አሸብር ታደሰ የሚባሉ ግን ምንም ዓይነት ቅሬታ ይዘው ለዞኑ መምህራን ማኀበር ያቀረቡበት ቀን እንደሌለ ምላሽ ከመስጠታቸው በተጨማሪ መምህሩ ላይ ማስፈራሪያና ዛቻ ፈፅመዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በወረዳው አንድ መምህር ግንቦት 1 ቀን 2005 ዓ.ም.  በኢህአዴግ አባል መምህር የድብደባ ወንጀል ተፈፅሞበት ክስ ሲመሰረት ደኢህዴን/ኢህአዴግ ክሱ ውድቅ እንዲደረግ ማስቻሉም ተጠቁሟል፡፡
   Posted By.Dawit Demelash

No comments:

Post a Comment