Friday, March 20, 2015

እናቶችን የሚያስለቅስ አገዛዝ

March 20th, 2015

የካቲት 10/2007 ዓም የ28 ቀን ጊዜ ቀጠሮ የተጠየቀበት የነዘመነ ምህረት ችሎት፣ በቀጠሮው መሠረት፣ ዛሬ መጋቢት 10/2007 ዓም ተሰይሟ። ዘመነ ምህረት፣ መለሰ መንገሻና ሌሎች ወደ 25 የሚጠጉ ወጣቶች በማእከላዊ ፓሊሶች ታጅበው 8:ሰአት 20 አካባቢ ፍርድ ቤት ግቢ ገቡ። እንደተለመደው በርቀት እጃቻችንን በማውለብለብ ሰላም አልናቸው። እነሱም ባልታሰረው እጃቸው አፀፋውን መለሱልን።


ዘመነ ምህረት ብዙም አልተጎሳቆለም። መለሰ መንገሻ ግን በጣም ከስቷል። ሰውነቱ ቢጫ ሆኗል። እንደዛም ሆኖ ፈገግታ ግን አልተለያቸው። ችሎት ከመግባታቸው በፊት የተቀመጡበት አግዳሚ ወንበር ላይ ሆነው፣ በምልክት ለመነጋገር ሞክረን ለመግባባት ችለን ነበር። ነገር ግን ፓሊሶች ከኛ ጋር የሚያደርጉት የምልክት መግባባት አይተው፣ ፊታቸውን አዙረው አስቀመጧቸው ። ተስፋ ሳንቆርጥ ሞከርን። አልተሳካም።


የችሎት ሁኔታ እንደሚታወቀው በዝግ የታየ በመሆኑ የነበረውን ሁኔታ ማወቅ አይቻልም። ዘመነና መለሰ መንገሻ ችሎት የገቡት ተለያይተው ነው። ከዚህ መረዳት የሚቻለው የተከሰሱበት መዝገብ ይለያያል ማለት ነው ። ሁለቱም ችሎት ሲገቡ ሌሎች ወጣቶች አብረዋቸው ገብተዋል።


የዛሬው የችሎት ሁኔታ ተጨማሪ የ28 ቀን ጊዜ ቀጠሮ ፓሊስ ጠይቆ ለመጋቢት 08/7007 ዓም ተቀጥሯል።
አንድነት ዘመነ ምህረት፣ የዘመነ ምህረት የበኩር ልጅ፣ በፍርድ ቤት አልተገኘም። የሕጻን አንድነትን ቦታ ተክተው፣ ከሰሜን ጎንደር ተጉዘው የመጡት፣ የቆራጡ ታጋይ ዘመነ ምህረት እናት ነበሩ። እኚህ እናት ታማሚ ናቸው። የወለደ አንጀታቸው አልችል ብሏቸው ህመማቸውን ችለው፣ ከሰሜን ጎንደር፣ ከ700 ኪሎሜትር በላይ ተጉዘው፣ «ልጄ በህይወት መኖሩን ካላየሁ አላምንም» ብለው፣ አራዳ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ተገኝተዋል። በጣም ያሳዝናሉ።


የመጡበትን ምክንያት የልጃቸውን በህይወት መኖር አለመኖር ለማረጋገጥ ነበር። በካቴና ታስሮም ቢሆን አይተዋል። በውስጣቸው ምን እንደተሰማቸው ባላውቅም። ጥልቅ የሆነ ሀሳብ ገብቷቸዋል። ለሰው ከመናገር ዝምታን ። ከኚህ የጀግና እናት ጋር ትንሽ ለመጨዋወት ሞክረን ነበር ። እንባቸው እየቀደማቸው ማውራት አልቻልንም። በመጦሪያቸው ጊዜ መንከራተት በጣም ያማል። እስኪ የኝህ እናት ፀሎት ተሳክቶ ዘመነ ተፈቶ ከመንከራተት 
ያድናቸው ዘንድ እንፀልይላቸው ።

http://www.abugidainfo.com/amharic/index.php/17639


No comments:

Post a Comment