Thursday, October 29, 2015

በአማራው ስም የሕወሓት ተላላኪ የሆኑ ሆዳም የብአዴን አመራሮች በአማሮች ላይ የሠሯቸው 14 እርጉም ግፎች

ተላላኪው ም/ል ጠቅላይ ሚ/ር እና የኢሕአዴግ ሊቀመንበር ም/ል ደመቀ መኮንን; ሕወሓት የሚሳደበው አንሶ የአማራውን ሕዝብ                ከተሳደቡት አቶ አለምነህ መኮንንና ከተላላኪ የአማራ የጦር መኮንኖች ጋር::

በትናንትናው እለት የብአዴን ምክትል ሊቀመንበርና የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ቃለምልልስ ሲያደርጉ ተከታተልሁ:: ርእሰ መስተዳድሩ ባንድ ወቅት “አማራ የራሱን የጦር ጀኔራል መርጦ ህዝቡን እያስታጠቀ ነው” በሚል በትግራዩ ገዥ አቶ አባይ ወልዱ ለቀረበባቸው ክስ “አዎ ለክልሌ ጀኔራል ነኝ” ብለው መልስ ሰጡ የሚል ጽሁፍ አንብቤ ስለነበር ልቤ በኩራት እብጥ ብሎ ክብር ሰጥቻቸው ነበር:: በአማራው ላይ የሚደርሰው ዘርፈ ብዙ ጥቃት ያበቃ ዘንድ በብአዴን ውስጥ ያሉት አማሮች በቁጭት “በወገኖቻችን ላይ የሚደርሰው ሰቆቃ በቃ!”ብለው ተነስተዋል ማለት ነው ብየ ገምቸ ነበር:: ምንም ቢሆን ልጅ የወላጆቹን ባህሪ መውረሱ አይቀርም: ይኸው የብአዴን አማሮች ያባቶቻቸውን ወኔ ተላበሱ ብየ በደስታ የምሆነውን አጥቸ ነበር:: ይሁንና ሰውየው በሰሞኑ ያደረጉት ቃለመጠይቅ ላይ ብአዴን የአማራ ህዝብ የዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶቹ ተከብረው ከሌሎቹ ወገኖቹ ጋር በእኩልነት እንዲኖር ከትምክህተኞችና ከጠባቦች ጋር ብዙ ትግል እንዳደረገና ውጤት እንዳስገኘ ሲገልጹ ሰማሁና ከልብ አዘንሁ:: አቶ ገዱ እናንተ የምታወሩትን ወይስ ምድር ላይ የሚታየውን እንመን? እንደእኔ እምነት የአማራ ህዝብ መቸም ቢሆን ያላገጠመውን ፈተና በናንተ ጊዜ እየተፈተነ ነው:: አማራ ተኮር የሆነ ጭፍጨፋ የተፈጸመውና ህዝባችን አጎንብሶ እንዲኖር የተደረገው በናንተ ጊዜ ነው:: ይህ ሁሉ መከራ በአማራው ላይ ሲፈጸም “ለምን እንዲህ ይሆናል” ብላችሁ ለመሟገት የሚያስችል እንጥፍጣፊ ወኔ የላችሁም:: እንዲያውም ድርጅታችሁ በተላላኪነት ተግባር ተሰማርቶ ግፍ አንገፈገፈን ብለው ተቃውሞ ያሰሙትን ወገኖች አሳዶ በመምታት የወያኔ አፋኝ ስኳድ ሆኖ እየሰራ ያለ ድርጅት እንደሆነ ህዝባችን አሳምሮ ያውቃል:: “የወጋ ቢረሳ የተወጋ አይረሳ” ነውና እስቲ በኢህአዴግ ጊዜ በአማሮች ላይ የተፈጸመውን ግፍና የናንተን አቋም በጥቂቱ እናስታውሳችሁ:-

1. በደርግ የመጨረሻ ዘመን አሶሳ ላይ አማሮች ብቻ ተለይተው ሲታረዱና በእሳት ሲቃጠሉ ድርጅታችሁ አንድም ተቃውሞ አላሰማም::

2. የናንተን ድርጅት ያካተተው ኢህአዴግ መላ ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረ በኋላ አማሮች እየተለቀሙ ከነነፍሳቸው በገደል ሲጣሉ:በገጀራ ሲታረዱ: በእሳት ሲቃጠሉ ድርጅታችሁ የወገንተኝነት ስሜት ተሰምቶት “ለምን ምንም ያላጠፉ ሰዎች አማራ በመሆናቸው ብቻ እንዲህ አይነት ግፍ ይፈጸምባቸዋል?” ብሎ በመቆርቆር እወክለዋለሁ የሚለውን ህዝብ መብት ለማስከበር ሲንቀሳቀስ አልታየም:: እንዲያውም ያሁኑ ፓስተር የያኔው የድርጅታችሁ ሊቀመንበር ታምራት ላይኔ በጅጅጋ ተገኝቶ በሶማሊያ ክልል በሚኖሩት አማሮች ላይ የሶማሌ መንግስትና ህዝብ እርምጃ እንዲወስዱባቸው በመቀስቀስ ድርጅታችሁ ጸረ አማራ መሆኑን እናንተም የጠላት ሀይል አንድ ክንፍ መሆናችሁን አስመስክሯል::

3. ከንጉስ ኃይለስላሴ ጊዜ ጀምሮ ለብሄር ብሄረሰቦች መብት መከበር: ለሰው ልጅ እኩልነትና ነጻነት እልህ አስጨራሽ ትግል ሲያደርጉ ከነበሩትና መስዋእትነት ክከፈሉት ሰወች መሀል የአማሮች ቁጥር ቀላል የሚባል አይደለም:: ይሁንና በነገስታቱና በደርግ ጊዜ በኤርትራ ላይ ተፈጽሟል ለተባለው ወንጀል አማሮችን ቀጥተኛ ተጠያቂ በማድረግ አስመራ ድረስ ሄደው “ማሩን” ብለው ከሻእቢያ እግር ላይ ወድቀው ይቅርታ እንዲለምኑ ሲደረግ “ለምን እንዲህ ይሆናል? ባለፉት ስርአቶች በገዥነት የተቀመጡ አማሮች ብቻ አልነበሩም: ታዲያ እንዴት አማራው ብቻ ይቅርታ ጠይቅ ይባላል?” ብላችሁ ለህዝባችሁ መብትና ክብር ያሰማችሁት ተቃውሞ አልነበረም::

4. አማራ ከየክልሉ ሀብት ንብረቱን ጥሎ የሞተው ሞቶ ማምለጥ የቻለው እግሩ ወዳመራው ሲሰደድ “አይደለም ኢትዮጵያ ውስጥ ሌላ ሀገር ውስጥ የሚኖር አማራ ካላግባብ ሀብት ንብረቱን ሊነጠቅ: ህይወቱን ሊያጣ አይገባም” ብላችሁ ስትከራከሩ አልተሰማችሁም:: ይባስ ብሎ የድርጅታችሁ የወቅቱ ሊቀመንበር አቶ አዲሱ ለገሰ ከኦሮሚያ የተባረሩትን አማሮች በተመለከተ ለተጠየቁት ጥያቄ ሲመልሱ የተባረሩት ሰዎች አጭበርባሪወችና ዘራፊወች ናቸው ነበር ያሉት:: የአማራ ሰዎች እንደዚያ በጅምላ ከየክልሎች አላግባብ እንዲፈናቀሉ ሲደረግ በአማራ ክልል ግን የሌሎች ክልሎች ተወላጆች በድርጅታችሁ ታቅፈውና ሹመኛ ሆነው በአማሮች ላይ እየፈረዱና ሀብቱን እየመዘበሩ በማናለብኝነት ቀጥለዋል:: ለዚህስ የምትሰጡት መልስ ምንድን ነው? የሚገርመው ደግሞ የአማራን ህዝብ ጥንብ እርኩሱን አውጥቶ ያዋረደው የክልሉ ተወላጅ አቶ አለምነው መኮንንን ህዝብን ያህል ነገር እንዴት እንዲህ ታረክሳለህ ተብሎ ሊጠየቅ ሲገባ እርስዎን ጨምሮ ሌሎች የድርጅቱ አባላት ባንድ ላይ ሰውየው የህዝብ ተቆርቋሪ እንደሆነና የተወራበት ሁሉ የጠላት ወሬ እንደሆነ ልታሳምኑን ስትደክሙ ሰምተን እጅግ አዝነናል:: በህዝብ ላይ ያን ያልተገረዘ የባለጌ መላሱን ያስረዘመውን ስድ አደግ ሰው ልትቀጡ ወይም ልትገስጹ ሲገባ ከህዝብ በላይ አድርጋችሁ በማየት የተገላቢጦሽ ለህዝብ የተቆረቆሩትን ሰዎች ወረፋችሁ::

5. በአማራ ክልል የሚኖሩ ብሄረሰቦች በዞን ተደራጅተው ራሳቸውን በራሳቸው እንዲያስተዳድሩ ሲደረግ አማሮች በብዛት በሚገኙባቸው ሌሎች ክልሎች ግን ይህ እድል አልተሰጠም: ሌላው ቀርቶ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን እንኳ በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው እንዲማሩ ዕድሉን አላገኙም:: ታዲያ እናንተ የታዘዛችሁትን ከመፈጸም አልፋችሁ እንዲህ የተዛነፈ አሰራር ሲታይ ምን ያደረጋችሁት ነገር አለ?

6. የአዊ ዞን ልጆቻቸው የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በአማረኛ እንዲማሩ ተስማምተው ያሳለፉትን ውሳኔ ከበላይ የመጣ ትእዛዝ ነው በሚል የብሄሩን መብት ገፍፋችሁ አዊወች በአዊኛ እንዲማሩ አደረጋችሁ: ይህን ውሳኔውን ያሳለፉትን ሰዎችም “የመንግስትን ፖሊሲ ተቃርነው የቆሙ” በማለት ፈርጃችሁ ከስራ እስከማባረር ድረስ የደረሰ ቅጣት ቀጣችኋቸው::


7. ለሱዳን ሊሰጥ በታሰበው መሬት ላይ የህዝብ ቁጣ ሲባባስ “የምንሰጠው መሬት የለም: ከሌላ የወሰድነውም የለም:: የራሳችን የሆነውን አንሰጥም የሌላውንም አንፈልግም” ብለው ነበር:: ይሁንና በተጨባጭ ከመተማና ካካባቢው በሱዳን ወታደሮች በሀይል እንደተፈናቀሉ ተፈናቃዮቹ አዲሳበባ ድረስ በአካል ተገኝተው ለፓርላማው አቤቱታ ማቅረባቸው በተጨማሪም ለአሜሪካው የአማረኛ ሬዲዮ ስርጭት (VOA) ቃለምልልስ መስጠታቸው አይዘነጋም:: አቶ መለስ ይህንን አስመልክቶ ከፓርላማው ለቀረባቸው ጥያቄ ሲመልሱ “አንድም ሰው አልተፈናቀለም” ብለው ሙልጭ አድርገው 
ዋሽተው ነበር:: እርስወም ድንበሩን በተመለከተ ለቀረበልወት ጥያቄ ከአቶ መለስ የተለየ መልስ አይደለም የሰጡት::

8. ከ10 አመት በፊት በተደረገው የህዝብ ቆጠራ ከሌሎች ክልሎች በተለየ መልኩ በአዲስአበባና በአማራ ክልል ብቻ ፕሮጀክት ከተደረገው ቁጥር በእጅጉ ማነሱ ይታወቃል:: በአዲስ አበባ ከሚኖረው ህዝብ መሀል እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለው አማራው መሆኑን ያጡታል ብየ አላስብም:: ታዲያ ይህ የአማሮች በ2.5 ሚሊዮን ቁጥር መቀነስ መላው ፍትህ ወዳድ ኢትዮጵያዊያንን በንዴት ሲያርገፈገፋቸው ብአዴን ግን አንድም ሰው እንዳልጎደለበት ሆኖ ማስተባበያ በአቶ አዲሱ ለገሰ በኩል ሲሰጥ ነበር::
9. በአማራ ክልል ላይ ብቻ ያተኮረ በቤተሰብ ዕቅድ ስም እየተፈጸመ ያለው የዘር ማጥፋት ወንጀል በወያኔ ተቀርጾ በናንተ የሚፈጸም አስነዋሪ ተግባር ነው:: የቤተሰብ ብዛትን መመጠን በሚል ምክንያት በአማራ ክልል ህዝብ ላይ ብቻ ያተኮረ የሴቶችን ማህጸን መቋጠር: የወንዶችን የዘር ፍሬ ማኮላሸት የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው:: አሁን ደግሞ ስልቱ ተቀይሮ የአማራ ሴቶችን የበሽታ መከላከያ ክትባት በማስመሰል መሀን የሚያደርግ መድሀኒት እንዲከተቡ ሲደረግ ብአዴን የወያኔን አላማ ለማስፈጸም ቀዳሚ ሆኖ የተሰለፈ ቡድን ነው::

10. አማሮችን ትጥቅ አስፈቱ የሚል መመሪያ በወረደላችሁ ጊዜ ምን ያህል ግፍ እንደፈጸማችሁ ትዝ ብሏችሁ ያውቃል? ወያኔ ይህን መመሪያ ሲያስተላልፍ ምክንያት እየፈጠረ አማሮችን ለመበቀል ካለው ፍላጎት በመነሳት ነበር:: ይህን ለማድረግ ደግሞ በራሱ ሰዎች ሳይሆን ህዝቡን እንወክለዋለን በምትሉት በናንተ ቢፈጸም ከተጠያቂነት ነጻ እንደሚሆን አሰበና “ህገወጥ መሳሪያ ታጣቂወችን መሳሪያቸውን እንዲያስገቡ አድርጉ” ሲል ትዕዛዝ ሰጣችሁ:: ይህን የበላይ ትእዛዝ ለማስፈጸም ነበር መሳሪያ ያልነበረውን ሳይቀር አስራችሁ የገረፋችሁት ብሎም የገደላችሁት:: የናንተ ህዝባዊነት መገለጫ የሰውን ክብር ገፋችሁ አባቶችን ሳይቀር ማሰቃየት ነው?

11. ለመሆኑ ቁልፍ በተባሉት የወታደራዊና የሲቭል ተቋማት ውስጥ የአማሮች ድርሻ ምን ያህል ነው? ይህስ አሳስቧችሁ ያውቃል? ወያኔ ገንዘብ የሚታፈስባቸውንና ስልጣንን ለማስጠበቅ የሚያስችሉ ተቋማትን ተቆጣጥሮ በቢሊዮን ዶላር የሚቆጠር ያገር ሀብት ዘርፎ ከሀገር ሲያስወጣ ምን ያደረጋችሁት ነገር አለ? የሀገር ሀብት ለሁሉም ክልሎች እንጅ ለአንድ ቡድን ብቻ አገልግሎት እንዳይሰጥ ለማድረግ የሰራችሁት ስራስ ምን አለ?

12. የብድርና የቁጠባ ወይም የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ አገልግሎት ለሁሉም አማራ ፍትሀዊ በሆነ መንገድ ነው የምታከፋፍሉት? አገልግሎት ማግኘት የህዝብ መብት ነው:: እናንተ በአመራር ላይ የተቀመጣችሁ አገልግሎት ለማግኘት ሳይሆን ያለአድልዖ አገልግሎት ለመስጠት ነው:: ግን እናንተ በተግባር እያደረጋችሁ ያላችሁት ምንድን ነው? የአማራው ህዝብ በሙሉ እንደናንተ ፍጹም የወያኔ ሎሌ ሆኖ የታዘዘውን እንዲፈጽም: ሲገድሉት እንዲሞት ለማድረግ ስንት ግፍ ሰራችሁ? ጠላትና ወዳጅ በማለት ከፍላችሁ እንደናንተ ሊሆን ያልፈቀደውን ሰላማዊ ዜጋ በተለያየ መንገድ አላሰቃያችሁም?

13. ህዝቡ የፖለቲካ አማራጭ የማግኘት መብቱ በህገመንግስቱ የተጠበቀ ነው:: ይህንን የህዝብ መብት አክብራችሁ ህዝቡ በመረጠው እንዲተዳደር ምን አድርጋችኋል? በግድ ውጣ ተብሎ እንዲመርጥ የተደረገን ህዝብ ምርጫውን ነፍጋችሁ እጅ እጅ በሚል ውሸት እኛ ተመረጥን ስትሉ የብዙሀኑን መብት የነፈጋችሁና በህዝብ ላይ በጉልበት የነገሳችሁ አምባገነኖች እንደሆናችሁ አስተውላችሁት ታውቃላችሁ? መቸ ነው ወደህሊናችሁ የምትመለሱት?

14. ክልሎች ታሪክ እየጠቀሱ የመሬት ይገባኛል ጥያቄ ሲያነሱ የአማራ ክልል ግን በግላጭ በታሪክ የሚታወቀውን መሬቱን ማስከበር አልቻለም:: አንዳንድ የዋህ ሰዎች በአንድነት እስከኖርን ድረስ አንድ አካባቢ በዚህ ወይም በዚያ ክልል ቢካተት ችግር የለውም ሲሉ ይደመጣሉ:: እንደእኔ ከሆነ ይህ አባባል ፍጹም ስህተት ነው:: የመገንጠል መብት በተከበረበት ሀገር ትክክለኛ የራስን መሬት ሳይዙ ህገመንግስቱን ማጽደቅ አደጋው ቀላል አይደለም:: ዛሬ እየኖርን ያለነው አንድነቷ በተጠበቀ ሀገር ውስጥ አይደለም:: ህገመንግስቱም ቢሆን በአንድነት ለመቀጠላችን ዋስትና የሚሰጥ አይደለም:: የፈለገውን ማድረግ እየቻለ ያለው ወያኔ የተፈራረምንበትን ህገመንግስት መሰረት በማድረግ ነገ ብድግ ብሎ ለመገንጠል ወስኛለሁ ቢል በምን ነው ልንከላከል የምንችለው? የክልል መንግስታት ተፈራርመው ያጸደቁት ህገመንግስት በአለም አቀፍ መድረክ ተቀባይነት የማይኖረው ይመስላችኋል? በርግጥ በአሁኑ ጊዜ ከትግራይ ውጪ ያሉት ክልሎች መገንጠል እንፈልጋለን የማለት ድፍረቱ አይኖራቸውም: ድፍረቱ ቢኖራቸው እንኳ ወያኔ ጥያቄውን ለማዳፈንና ጥያቄ አቅራቢወችን ለመበቀል የሚሄድበት መንገድ አያጣም:: ነገር ግን የወያኔ ፈቃድ ሆኖ ክልሎች እንዲገነጣጠሉ ቢያደርግ ታሪካዊ መሬታችን ነው የምንለውን አካባቢ እንዴት ነው ማስመለስ የምንችለው? የአማራ ክልል ለመሆኑ ታሪካዊ መኖሪያ አካባቢው የቱ ነው? ይህ ጥያቄ ከተመለሰ በኋላ ነበር ህገመንግስቱ ቢፈረምም መፈረም የነበረበት:: ድርጅታችሁ አላግባብ የተወሰደበትን መሬት ለማስመለስ ያደረገው ምን ነገር አለ? “አማራ ነን:: ያላግባብ ወደትግራይ ክልል እንድንካተት ተደርገናል” እያሉ ለሚጮሁት የወልቃይት ወገኖቻችንስ ምን አደረጋችሁ? ታዲያ ለአማራው ህዝብ መብትና እኩልነት ያደረጋችሁት የሚያስፎክር ትግል የት አለ!

በርግጥ ማንም አሌ የማይለው ነገር ቢኖር አማራው ሀገሩ ኢትዮጵያ መሆኗን ነው: የኖረውም የሀገሪቱን ዳር ድንበር ለማስከበር: ሰላምና ጸጥታ ለማስፈን በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢወች ነው:: ይህችን ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር አስከብሮ ለእኛ ያስረከበ ህዝብ እንደጠላት እየታደነ ሲገደል አባሪ ከመሆን ውጭ ለክልሉና ለህዝቡ ያበረከታችሁት አንድም አኩሪ ስራ የለም:: እናንተ የአማራውን ህዝብ የምታኮሩ ሳትሆኑ የምታሳፍሩ: የምታስከብሩ ሳትሆኑ የምታዋርዱ ሙሉ ትኩረታችሁን በሰፈር እየተደራጃችሁ ስልጣን ለመያዝ በርስ በርስ ሽኩቻ ጊዜአችሁን የምታባክኑ እንጥፍጣፊ ህዝባዊ ስሜት የሌላችሁ የምትገርሙ ሰዎች ናችሁ:: አይናችሁን ጨፍናችሁ በምትዋሹት ውሸት የአማራው ህዝብ አምኖ ይቀበለናል ብላችሁ አስባችሁ ከሆነ ተሳስታችኋል:: ብታምኑም ባታምኑም ህዝቡ እናንተን ህሊና የሚባል ነገር የሌላችሁ የወያኔ ጉዳይ አስፈጻሚ ሮቦቶች እንደሆናችሁ አድርጎ ነው የሚያያችሁ:: ወያኔም ቢሆን በፈለገው መንገድ ሊያሰልፋችሁ የሚችል ጅሎች አድርጎ እንደሚያያችሁና እንደሚታዘባችሁ አንጠራጠርም::

ሰሞኑን አቶ ኃይለማርያም ከፓርላማ ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሲሰጡ የዶ/ር ደብረጽዮንን ስሜት ሳትገነዘቡ የቀራችሁ አይመስለኝም:: መቸም ኃይለማርያም ከራሳቸው የፈለቀች አንዲትም ቃል ሊናገሩ ድፍረት ይኖራቸዋል ተብሎ አይታሰብም:: ታዲያ ለሚቀርብላቸው ጥያቄ በወያኔ ተዘጋጅቶ የተሰጣቸውን መልስ ሸምድደው ገብተው “መንግሥታችን ርምጃ ይወስዳል…” ምናምን ሲሉ ዶክተሩ ስሜታቸውን መቆጣጠር አቅቷቸው የፌዝ ፈገግታ ሲያሳዩ ነበር:: ዶ/ር ደብረጽዮን “ነገ ቃላችንን አጥፈን ተቃራኒውን ለማድረግ ብንወስንና ይህንን ባደባባይ ተናገር ብንለው ያው እንደለመደው መንግስታችን እንዲህ ያደርጋል እያለ መናገሩ አይቀርም:: የነዚህ ሰዎች ሰውነት ከምኑ ላይ ነው?” የሚል አይነት የግርምት ፈገግታ ነበር ሲያሳዩ የነበሩት:: ወያኔ እንዲህ የሚያሾፈው በሁላችሁም ላይ ነው::


አማራን የሚያህል ትልቅና ታሪካዊ ህዝብ እንወክላለን ብላችሁ ግን ለውርደትና ለእልቂት ስትዳርጉት: ለዚህ ውለታችሁ የሚሰጣችሁ ክፍያ በአናሳው ቡድን እንዲህ መሳቂያ መሳለቂያ መሆን ከሆነ ምን አይነት ህሊና ቢኖራችሁ ነው አሜን ብላችሁ ተሸክማችኋቸው የምትኖሩት:: “አማራ ሆዳም ነው” እንደሚሉን እናውቃለን:: የህዝብ ክብርና ነጻነት ከምንም በላይ አይደለም እንዴ! ባትበሉት ባትጠጡት ባፍንጫችሁ ቢወጣ ምን ነበረበት::

እስከቀበሌ ድረስ በዘለቀው አደረጃጀታችሁ ተጠቅማችሁ “መላው የአማራ ህዝብ ሆይ ደምና አጥንት ከፍለህ ባስከበርሀት ሀገር ላይ መኖር ተከልክለህ ዘርፈ ብዙ ግፍ እየተፈጸምብህ ስለሆነ ይህንን ባንተ ላይ ያነጣጠረ ሰቆቃ ለማስወገድ ከጎናችን ተሰልፈህ መብትህን እንድታስከብር ጥሪያችንን እናስተላልፋለን::” የሚል አዋጅ ብታስነግሩ አማራው “ሆ” ብሎ ተነስቶ የተበላሸውን ለማስተካከል ጊዜ ይፈጅበት ነበር!

ለነገሩ ወያኔ ከራሱ ክልል ውጪ ላሉት ክልሎች ባለስልጣናትን ሲያስቀምጥ በተጠና መንገድ ሆድ እንጅ ህሊና የሌላቸውን ስለህዝብና ስለሀገር ደንታ ቢሶችን መርጦ ነው:: ለዚያም ነው አማራው ከያለበት እየተያዘ ግፍ ሲፈጸምበት አንድም ተቃውሞ ያላሰማችሁት! እናንተም ብትሆኑ አፋችሁ ያውራ እንጅ ለህዝብ ቀርቶ ለራሳችሁ እንደማትሆኑ ልባችሁ አሳምሮ ያውቃል:: ሙሉአለም ሲገደል ምን አደረጋችሁ? ታምራት ላይኔ በአደባባይ “በትግል ያልተሸነፈ ሰው በስኳር ተሸንፎ እጁን ሰጠ” ተብሎ ሲቀለድበት: ራሱን አዋርዶ “ቢመክሩኝ አልሰማ ብየ” ብሎ ቀበጣጥሮ ይቅርታ እንኳ ተነፍጎት ወህኒ ሲወርድ ከማጨብጨብ ውጪ ምን ሰራችሁ? ለነገሩ እንደፖለቲከኛ ሳይሆን እንደሆደ ቡቡ ህጻን በፍርሀት የቀባጠረ ሰው ሲመራው ከነበረ ድርጅት ምን ይጠበቃል?


የጊዜ ጉዳይ ነው እንጅ እናንተም ሆናችሁ ጌቶቻችሁ ከፍርድ አታመልጡም: የውሻን ደም ከንቱ የማያስቀር ግፍን የሚቆጥር አምላክ አለ:: እስከዚያው ድረስ እናንተ ስልጣን ላይ ተቀምጣችሁ ለምታገኙት ፍርፋሪ አማራውን ረግጣችሁ እንድትይዙ የእድል በር የከፈተላችሁን የልደት ቀናችሁን በፌስታ ስታከብሩ እኛ ደግሞ ያችን የተረገመች ቀን በሀዘን እናስታውሳታለን:: መቸም ከአንጎል ክፍላችሁ የሆነ የጎደለ ነገር አለ መሰለኝ ጸጸትና ቁጭት ይሰማችኋል ብየ አላምንም:: የህዝብን አስተያየት በግብአትነት ተጠቅማችሁ ራሳችሁን ወደውስጥ አይታችሁ ስህተታችሁን ለማረም ከመሞከር ይልቅ የሚተቿችሁን ለማጥፋት የምትተጉ እንደሆናችሁ ግን እናውቃለን:: እስካሁን በሰራችሁት ስራ ክብር ያገኛችሁ መስሏችሁ ከሆነ ተሳስታችኋል:: እና ሞኝ ባያፍር የሞኝ ዘመድ ያፍር ነውና በስራችሁ ከማፈርና ከማዘን አልፈን ምነው ሳትወለዱ በናታችሁ ማህጸን ውስጥ ውሀ ሆናችሁ በቀራችሁ ነበር ብለን ድርጅታችሁ የተወለደበትን ቀን ብቻ ሳይሆን እናንተ የብአዴን ሰዎች እራሳችሁ የየተወለዳችሁበትን ቀን ሳይቀር እረግመናል::

 http://www.zehabesha.com/amharic/archives/47815

No comments:

Post a Comment