Wednesday, October 28, 2015

በኢትዮጵያ ሰላምና መረጋጋት አለ” የሚለው ተረት ተረት ነው ሲሉ ዶ/ር መረራ ጉዲና ገለጹ


ጥቅምት ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኦሮሞ ፌደራሊስት ሊቀመንበር እና የመድረክ የአመራር አባል የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና ይህን ምላሽ የሰጡት ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ለተቃዋሚ ፓርቲዎች የቀረበውን የውይይት ግብዣ ተቃዋሚዎች ውድቅ ማድረጋቸውን ለፓርላማ አባላት መናገራቸውን ተከትሎ ነው።

መንግስት በጠራው የአምስት ኣመታት የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውይይት ላይ ያልተሳተፉ እንደመድረክ፣ ሰማያዊ እና መኢአድ ያሉ ፓርቲዎች ያቀረቡት ምክንያት ውሃ ያማያነሳ ነው ያሉት አቶ ሃይለማርያም ፣ ፓርቲዎቹ ያልተሳተፉት በሕጋዊ መንገድ የተመረጠ መንግስት አይደለም በማለት መሆኑን ጠቅሰው ወደፊት ከየትኛው መንግስት ጋር እንደሚወያዩ እናያለን ሲሉ ዝተዋል፡፡

ዶ/ር መረራ ሲናገሩ፣ “በቅድሚያ አንነጋገርም አላልንም፣ ቅድሚያ መሰረታዊ በሆኑት የአገሪቱ ጉዳዮች ላይ ለምሳሌ ነጻ ምርጫን ፣ ነጻ ሚዲያን፣ በነጻነት መንቀሳቀስንንና በመሳሰሉት መሰረታዊ መብቶች ጉዳይ እንነጋገር ” ነው ያለው ካሉ በሁዋላ፣ እነሱ በሚሉት ጉዳይ ላይ ለመነጋገርም ፣ በር ዘግቶ ሳይሆን፣ በነጻ ሜዳ፣ ለህዝብ በቀጥታ በሚተላለፍ መልኩ መሆን አለበት በማለት በጽሁፍ መግለጻቸውን ተናግረዋል።

መድረኩን ተጠቅማችሁ ለምን ሃሳባችሁን ለማስተላለፍ አልቻላችሁም በሚል ለተጠየቁት ዶ/ር መረራ፣ የኢህአዴግ ፖሊሲ ስልጣን ወይም ሞት በመሆኑ፣ የልጅ ስራ መጫወቱ ትርጉም የለውም ብለዋል።

አገሪቱ አደጋ ውስጥ ናት ያሉት ዶ/ር መረራ ዲሞክራሲው የፖለቲካ ቅርቃር ውስጥ መግባቱን፣ አገሪቱ ወደ አልተፈለገ አቅጣጫ እያመራች መሆኑዋንና የሚባለው ዲሞክራሲ፣ ሰላምና መረጋጋት አለመኖሩን እንዲሁም ረሃብና ድህነት ታሪክ ሆኗል የሚባለውም ተረት ነው በማለት ገልጸዋል።

http://www.satenaw.com/amharic/archives/10863

No comments:

Post a Comment