Sunday, October 11, 2015

ለብይን ተቀጥረው የነበሩት ዞን 9 ጦማሪያን ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቀሩ

በተጠረጠሩበት የሽብርተኝነት ድርጊት ወንጀል ለብይን ለመስከረም 27 ቀን 2008 ዓ.ም. ተቀጥረው የነበሩት ጦማሪያን ናትናኤል ፈለቀ፣ አጥናፉ ብርሃኔ፣ አቤል ዋበላና በፈቃዱ ኃይሉ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቀሩ፡፡

ጦማሪያኑ ፍርድ ቤት ያልቀረቡበት ምክንያት ደግሞ በዕለቱ በሌላ ሥራ ምክንያት ይሁን ወይም በሌላ ጉዳይ ባይታወቅም፣ ለብይን የቀጠሯቸው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዳኞች እንደሌሉ ተነግሯቸው መሆኑ ታውቋል፡፡

ብይኑ በዕለቱ እንደሚሰጥ የገመቱ የጦማሪያኑ ቤተሰቦች፣ ጓደኞቻቸውና ጋዜጠኞች በፍርድ ቤቱ ቅጥር ግቢ የተገኙ ቢሆንም፣ የፍርድ ቤቱ ሠራተኞች ‹‹ዳኞች ስለሌሉ እንዳይመጡ መስከረም 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ለማረሚያ ቤቱ ተደውሎ ተነግሮታል›› በማለታቸው ለመከታተል የሄዱ ታዳሚዎች ተመልሰዋል፡፡

የጦማሪያኑ ጠበቆች ግን በሁኔታው ማዘናቸውን ተናግረዋል፡፡ ቢያንስ ቢያንስ ፍርድ ቤቱ በማስታወቂያ ሰሌዳ ላይ ማስታወቂያ መለጠፍና ጉዳዩን የሚከታተሉ እንዲረዱ ማድረግ ሲገባው፣ ምንም ሳይል መሄዱ አግባብ አለመሆኑንና ታይቶም እንደማይታወቅ ገልጸዋል፡፡


ጦማሪያኑ እንዲከላከሉ ወይም መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ የሚሰናበቱበት ብይን ጥቅምት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ዳኞች በሙሉ ከመስከረም 26 ቀን እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. አዳማ ሥልጠና ላይ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/47329

No comments:

Post a Comment