Thursday, July 10, 2014

ሰላማዊ ዜጎችን ማሰር የሽንፈትና የደካማነት ምልክት ነው

july.10.2014

አገር ቤት ያሉ መሪዎች ቁርጠኝነት ያስደንቀኛል። ግርማ ሰይፉ «ለመታሰር እንዘጋጅ» አለ። ዳንኤል ተፈራ «ገዥዎች፣ እመኑኝ ባሮጌው መንገዳችሁ በርካቶችን ነፃነት ናፋቂዎች በሰፋፊ እስር ቤታችሁ ታጉሩ ይሆናል፡፡
ነገር ግን የዚህን ትውልድ የነፃነት መንፈስ ግን ልታስሩት አትችሉም» አለ። የፍኖት ዋና አዘጋጅ ነብዩ «ጨቋኞችን መታገል ፅድቅ እንጂ ኩነኔ እንደሌለው አምናለሁ፤ ጭቆናን እምቢ በማለቴ የምጠጣት እያንዳንዷ ፅዋ በፈጣሪ ዘንድ ወሮታ እንደምታከማችልኝም አምናለሁ፡፡ ፍርሀትን ብቻ እፈራለሁ» ሲለን፣ የአዲስ አበባ አንድነት ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ ያሬድ አማረ ደግሞ «ወደኋላ አንመለስም። ዘመን ተሻጋሪ ወጣቶች በቅለናልና በምንም መልኩ ለሚደረግ ማዋከብ፤ እስራት እና ግድያ ከጀመርነው የሰላማዊ ትግል መስመር ስንዝር አያዘንፈንም፡፡ ደግሞም አምባገነኖች ባሉበት ሀገር የጀግና ቤቱ እስር ቤት አልያም መካነ መቃብር ውስጥ ሊሆንም እንደሚችል ስንጀምር ያለአስረጂ እናውቃለንና» በማለት የትግሉ ደረጃ ምን መስመር ላይ እንዳለ እቅጩን ይነግረናል።
አንድነት እና መኢአድ ሊዋሃዱ ዝግጅት ላይ ናቸው። በየክልሉ ሕዝቡ በሰላማዊ ሰልፎች ተቃዉሞዉን እያሰማ ነው። ሂዱ አዳማ፣ ሂዱ ወላይታ፣ ሂዱ ጎንደር፣ ሂዱ ደሴ ፣ ሂዱ ጂንካ፣ ሂዱ ጊዶሌ ….ሕዝቡ «በቃን፣ መረረን« እያለ ነው። ለ23 አመት የተዘራዉን የዘር መከፋፈል አረም እየነቀለ አንድ ነን እያለ ነው። «ኦሮሞ፣ አማራ፣ ትምህክተኛ፣ ጠባብ….እያላችሁ አትከፋፍሉንም» እያለ ነው። የሚሊዮኖች ንቅናቄ ተጧጡፎ እንደሚጧጧፍ፣ የመኢአድ እና አንድነት ዉህደት በስኬት እንደሚጠናቀቅ፣ የምርጫ ዘመቻና ዝግጅት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል፣ የአንድነት አመራሮች እየነገሩን ነው። አገዛዙ ዜጎችን በማሰር ትኩረት ለማስቀየር የሚያደርገውም ደባ አይሳካለትም።
ትላንት ብርቱካንን ሲያስሩ ያበቃ መሰሏቸው ነበር። ትላንት እስክንድርን ሲያስሩ ያበቃ መሰላቸው ነበር። ትላንት ርዮት አለሙን ሲያስሩ ያበቃ መሰላቸው ነበር…..ግን ተሳሳቱ። እነ ሃብታሙ አያሌው ፣ አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ዳንኤል ሺበሺ፣ ዞን ዘጠኖች ….ብቅ አሉ። እነርሱን ደግሞ በጭካኔ እየደበደቡ ወደ ማእከላዊ ወሰዱ። ሚሊዮኖች ግን ድምጻቸውን እያሰሙ ነው። «የነፃነት ታጋዮችን በማሰር የወጣችው የኢትዮጵያዊነት ፀሀይ ትደምቃለች እንጂ አትጠፋም» እንዳለ ዳዊት ሰለሞን ፣ ገዥው ፓርቲ ሰላማዊ ዜጎችን ማሰሩ ደካማነቱን፣መክሰሩን፣ መሸነፉን ፣ መደንገጡን በአንድ በኩል እያመላከተ በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ትንሳኤ መቅረቡን የሚያሳይ ነው።
አንድ በሳል መሪ፣ ችግሮች ሲፈጠሩ፣ ችግሮቹን በዉይይት፣ ሌሎችን በማሳመን፣ ኮምፕሮማይዝ በማድረግ ለመፍታት ይሞክራል። ያኮረፈዉን፣ የሚቃወመዉን፣ ሸፍቶ ነፍጥ ያነሳዉን ለማግባባትና ወደ እርሱ ለማምጣት ይሞክራል። ተቃዉሞ የሚያቀርቡትን፣ የተለያየ ስም እየሰጠ ለማጥፋት አይሞክርም። የኢሕአዴግ መሪዎች፣ እያደረጉ ያሉት ነገር ቢኖር ግን፣ አንድ በሳል መሪ ማድረግ ያለበትን ሳይሆን፣ የአንድነት ፓርቲ መግለጫ እንዳስቀመጠው፣ መንግስታዊ ዉንብድናን ነው። መንግስት እንደ አባት ነበር የሚታየው። ዜጎችን ማክበር፣ ማገልገል ይጠበቅበታል። የዜጎችን ጥቅም በአገር ዉስጥ ሆነ ከአገር ዉጭ ለማስከበር ይተጋል። የኛዎቹ የኢሕአዴግ መሪዎች ግን፣ ዜጎችን እያሸበሩ ነው። ኢትዮጵያዉያንን እያስፈራሩና እያዋረዱ ነው። ጨካኞች፣ ግትሮች፣ ለሰብእና ከበሬታ የሌላቸው፣ ሕግን እየጠመዘዙ፣ ፍርድ ቤቶችን በካድሬ ዳኞች እየሞሉ፣ የዉሸት ምስክር እያቀረቡ ዜጎችን የሚያንገላቱ፣ ያለነርሱ አዋቂ፣ ያለነርሱ ኢኮኖሚስት፣ ያለ እነርሱ ኢንጂነር፣ ያለ እነርሱ የሕግ አዋቂ ያለ አይመስላቸውም። እነርሱን የሚቃወም ሁሉ «አሸባሪ» ነው።
ኤሚ ሰለሞን የምትባል ብሎገር «ጋዜጠኞችና ጦማሪያን ለምን ጻፋቹህ ? ለምን ያገባናል አላችሁ ? ተብለው በየእስር ቤቱ የታጎሩትና በየጊዜው እያንጠለጠሉ የሚወስዷቸው ስንት ናቸው ? ስንቱን ከሃገር አሰደዱ ? ማነው አሸባሪው ታዲያ ?» ብላ እንደጠየቀቸው፣ በአገራችን የሽብር ተግባር እየፈጸመ ያለው ኢሕአዴግ እራሱ ነው።
«እፎይ! ካሁን በኋላስ መቼም ቢሆን ከደርግ የከፋ መንግስት ሊመጣ አይችልም’ ብለን ነበር። ከ23 ዓመት በፊት . .» እንዳለው ኩሪ ሀገሬ የተባለ ብሎገር፣ ከ23 አመት በፊት፣ ብሶት የወለደው የኢሕአዴግ ሰራዊት ፣ አዲስ አበባ ሲገባ እና ለሰፊዉ ሕዝብ ጥቅም የኢትዮጵያን ራዲዮን እና ኢቲቪ ሲቆጣጠር ፣ ቢያስን የተሻለ ነገር ይመጣል ብለን ነበር። ዳሩ ግን ቅሉ፣ ከፈረንጆች በልመና በተገኘ ገንዘብ ግንብና ፎቅ እየሰሩ፣ ክብራችንን፣ ስብእናችንን፣ ነጻነታችን ገፈው በአገራችን ባሪያ ሊያደርጉን የሞት ሽረት እንቅስቃሴ እያደረጉ ነው።
ነገር ግን አሁን ከ10 አመት፣ ከ15 አመት በፊት እንደነበረው አይደለም። ሕዝቡ መሮታል። የግፍ ቀንበርን ለመታገስ አይችልም። ኢትዮጵያ እሳት የለበሱ፣ ወኔ የሞላባቸው፣ ነፍጥ ሳይጨብጡ ጀግንነት ለመስራት የተዘጋጁ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዳግማዊ ጣይቱዎች አሏት። በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዳግማዊ ባልቻ አባ ነፍሶዎች አሏት። የሚሊዮኖችን ኃይል ደግሞ ሊቋቋም የሚችል ምንም ኃይል አይኖርም።
http://www.abugidainfo.com/amharic/index.php/15164

No comments:

Post a Comment