Saturday, December 7, 2013

ከወያኔ ምን አተረፍን ?


ከተስፋየ ታደሰ (ኖርዌ)
ኢትዮጵያ ሃገራችን 3000 ሺህ ዘመን ታሪክ ባለቤት ብትሆንም ያለመታደል ሆነና ዛሬ ድርስ ጥሩ መሪ አላገኘችም። ወያኔ የደርግን ስረዓት ጥሎ የስልጣን ኮርቻዉ ላይ ሲቀመጥ ሰፊዉ የኢትዮጵያ ህዝብ አሜን ብሎ ተቀብሎት ነበር። አበው ሲተርቱ እዉነትና ንጋት እያደር ይጠራል እንደሚሉት የወያኔ ድብቅ የፖለቲካ አጀንዳ እያደር ፍንትው ብሎ መታየት ጀመረ። ዘር ከዘር መለያየትና ማጋጨት ለከፋፍሎ መግዛት ፖሊሲው ይመች ዘንድ፣ በእምነት ላይ ጣልቃ መግባት እንዲሁም ለዘመናት በመቻቻል የሚታወቁትን ሁለቱን ታላላቅ ሃይማኖቶች ክርስቲያኑን ከሙስሊሙ ጋር ማጋጨት እንዲሁም በምርጫ የህዝብ ድማፅ መስረቅ የፖለቲካ ተቃዋሚዎችን ማፈን፣ ማሰር፣ ማሳደድ እንዲሁም መግደል ዋና ዋናዎቹ ናቸው። በወያኔ ስረዓት በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ተንሰራፍቶ የሚገኘዉ ከመቼዉም ጊዜ በላይ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ ድህነት፣ ጉስቁልናና ስራ-አጥነት ናቸዉ።ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ፍትህ በሌለበት በአጠቃላይ ፍትህ ዲሞክራሲና መልካም አስተዳደር በተነፈገበት ሃገር ህዝብን ማእከል ያላደረገ ልማትና እድገት ይኖራል ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው፡፡ በስልጣን ላይ ያለው ቡድን የራሱን ጉድ ለመሸፈን ሲል ኢትዮጵያ አድጋለች፣ ሁለት አሃዝ እድገት አስመዝግባለች፣ ረሃብ የለም ወዘተ….እያለ ነጋ ጠባ በአሸብራቂ ቃላት የአለም ማህበረሰብን ቀልብ በመሳብና ለማደናበር ይሞክር እንጂ በመሬት ላይ የሚታየው ሃቅ ግን በተቃራኒው ነው፡፡ በተለመደው መሰሪ ፕሮፓጋንዳው አይናችሁን ጨፍኑና ላሞኛችሁ ይበለን እንጂ የኑሮን ውድነት፣ መልካም አስተዳደር እጦት ምክንያት በረሃብ እየተቀጣ ያለው የኢትዮጵያ ህዝብን ማታለል ግን በፍጹም አይችልም፡፡ በተለይም ያልበላውን በልቷል፣ ያልሰማውን ሰምቷል ነጻ ወጥቷል የስርአቱ ልዩ ተጠቃሚ ሆኗል ወዘተእየተባለ ለአመታት በስሙ ሲነገድበት የኖረው የኢትዮጵያ ህዝብ ኑሮው በጣም ከባድ እንደሆነ ላይ የተገለጹ እውነታዎች ይመሰክራሉ።
ዛሬ በዚህ አስከፊ ስርአት ሳቢያ ከአንድ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተመርቆ የወጣ በእዉቀቱ ሳይሆን የኢህአዴግ አባል ካልሆነ የመንግስት ስራ አያገኝም ገበሬው ሰፊ የእርሻ ቦታውን እየተነጠቀ ለባዕድ ኢንቨስተሮች በሊዝ እየቸበቸበ ገበሬዉን ለድህነት ለጉስቁልና እየዳረገው ይገኛል። ወያኔ የዛሬ አስራ አምስት ዓመት ገደማ በመጪዉ አስርት አመታት የኢትዮጵያ ህዝብ በቀን ሶስት ጊዜ ይመገባል እንዲሁም የምግብ ዋስትና ይጠበቃል ብሎ ነበር ነገር ግን በየዓመቱ ከሰባት ሚሊዮን ህዝብ በላይ በረሃብ አለንጋ እየተጠበሰ ይገኛል። ሰብአዊነት ያልተላበሰ መንግስት ቢኖር እንደ ወያኔ ያለ መርዝ መንግስት ይኖራል ብሎ መናገር በጣም ያዳግታል። በአለም አቀፍ ግብረ ሰናይ ድርጅቶችና መንግስታቶች ምክንያት ለተረጂዉ የመጣዉን እህል አረመኔው የወያኔ መንግስት በምስኪኑ ተረጂ ወገን ጉሮሮ ላይ ቆሞ ለስግብግብ ነጋዴዎች አየር በአየር እየቸበቸበ የግል ኪሱን እያደለበ ይገኛል።
ሀገራችን ነፃ ጋዜጠኞችን በማሰርና በማፈን ከአፍሪካ ቀዳሚ ደረጃን ከያዙ ሃገሮች ተርታ መሰለፏ ይታወቃል ይህ ደግሞ የመናገር የመፃፍ መብትን የሚጋፋና የሚፃረር ተግባር መሆኑ ግልፅ ነዉ፤ በሌላ አለም ባልታየ መልኩ በኤሌትሮኒክስ መገናኛዎች መረጃ ተለዋዉጣችኋል፣ መንግስት የሚተች ፅሁፍ ጽፋችኋልና ለኔ አልተመቻችሁኝም የሚል ቅኝት ያለዉ ዉንጀላ በማቀነባበር ሽብርተኛ የሚለዉን ፀያፍ ስያሜ በማሸከም ዜጎችን ለእስርና ለስደት እንዲሁም የቀረዉን ለፍረሀት የሚዳርግ ሽብርተኛ ስረአት ነዉ ተሸክመን ያለነው። በተጨማሪም በነፃነት መደራጀት እና መንግስትን መቃወም አንድም ለእስራት አልያም ለስደት እየዳረገ ይገኛል፡፡ በርካታ ጋዜጠኞች፣ ወጣት ፖለቲከኞች፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እና ነጋዴዎች በነጻነት የመኖር፣ በነፃነት የመናገር እና የመፃፍ መብታቸው እየተገፈፈ በየእስር ቤቱ እየተሰቃዩ ይገኛለ፡፡ አሁን በሃገራችን በደልና ጭቆና በዝቷል ድህነትና ጉስቁልና ከመቸዉም በባሰ ተንሰራፍቷል እስርና ሰቆቃ ተራ ነገሮች ሆነዋል በአሸባሪዎች ስም እራሳቸዉ ቦንቦች አጥምደው ህዝቦች እየፈጁ ሰላማዊ ዜጎች በአሸባሪነት እየተፈረጁ ለስቃይ እየተዳረጉ ነዉ። ዛሬ በሃገራችን አርሶም ሆነ ነግዶ መኖር አይቻልም። መኖር የሚቻለዉ ኢሕአዴግ ልማት ነዉ የሚለዉን መዝሙር በመዘመር ብቻ ነዉ።
ባጠቃላይ ስረዓቱ ፀረ- ዲሞክራሲና ፀረ- ፍትህ አቋም የሚያራምድ ነዉ። በመሳሪያ የያዘዉን ስልጣን በዲሞክራሲና በፍትህ ለሚያምን ኢትዮጵያዊ ዜጋ እንዲያስረክብ እና የነፃነት አየር እንዲተነፍስ ስለ ሀገራቸዉ በመቆርቆር በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ሳይሸማቀቁ ጊዜና ሰአት እንዲሁም ቦታ ሳይገድባቸዉ የመናገር፣ የመፃፍ ጥያቄ ፣የመጠየቅ መብታቸዉ ተከብሮ አለም ከደረሰበት የእድገት ደረጃ ላይ ለማድረስና ከቂም በቀል የፀዳች አገር ለመጭዉ ትዉልድ ለማቆየት ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ ስልጣን ላይ ያለዉን ጨቋኝና -ዲሞክራሲያዊ የሆነና አንባገነናዊ ገዥ ፓርቲ አዉርዶ በምትኩ ዲሞክራሲያዊ የሆነ እና በበለጠ መልኩ የሁላችንን ነፃነት እና እኩልነት የሚያከብር መንግስት ለመተካት በሚደረገዉ ትግል ላይ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የአገሪቷን እድገት ጎዳና በአንድ ላይ ሆኖ እንዲንቀሳቀስ ጥሪዬን አቀርባለሁ። አገራችንን ከወያኔ ዘረኝነት አገዛዝ ነፃ ለማዉጣት ትግላችንን በማንኛዉም መልኩ ልናጠናክር እንደሚገባን በኢትዮጵያ ስም በድጋሚ አሳስባለሁ።
ድል ለጭቁኑ የኢትዮጵያ ህዝብ!!!

 Posted By.Dawit Demelash

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/10587

No comments:

Post a Comment