Thursday, September 29, 2016

በጎንደር እና ጎጃም የሚታፈሱ ወጣቶች አያያዝ ከፍተኛ ስጋት በውስጡ ፈጥሯል

በደብረ ማርቆስ እና ጎንደር በርካታ ወጣቶች በአፈሳ መታሰራቸው ተነገረ፡፡ አሁንም ድረስ አንጻራዊ መረጋጋት በሌለባቸው የሰሜናዊ ምዕራብ አማራ ክልል ከተሞች፣ የመንግስት ወታደሮች በተለይ ወጣቶችን በዘመቻ መልክ እያፈሱ መሆኑን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ በደብረ ማርቆስ ከተማ ወጣቶች ለመስቀል በዓል የሚዘምሩትን የመዝሙር ግጥም እስከማስለወጥ የደረሱት የመንግስት ወታደሮች፣ በዚህም ምክንያት በነዋሪው እና በደህንነቶቹ መካከል ግጭት መከሰቱን ከስፍራው የተገኘው መረጃ አመልክቷል፡፡

ግጭቱን ተከትሎ ቁጥራቸው በርከት ያለ ወጣቶች መታሰራቸውን የሚገልጹት የአካባቢው ነዋሪዎች፣ ወታደሮቹ የደመራውን በዓል ለማሰሪያነት እንደ ሰበብ ተጠቀሙበት እንጂ፣ እነማን መታሰር እናዳለባቸው አስቀድሞ ከቀበሌ አስተዳዳሪዎች ጋር መምከራቸውን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ለዚህም ነው በበዓሉ ወቅት ራሳቸው ሁከት እንዲፈጠር አድርገው ልጆቹን ያሰሯቸው›› ሲሉ ነዋሪዎቹ አክለዋል፡፡

በተመሳሳይ ሁኔታ በጎንደርም ብዙ ወጣቶች በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን፣ የሰሜን ጎንደር ከተሞችም በህወሓት ጥርስ ውስጥ መግባታቸውን ነዋሪዎቹ ገልጸዋል፡፡ የጸጥታ ኃይሎቹ በሰሜን ጎንደር ከተሞች ሰማይ ላይ ሄሊኮፍተር እያጓሩ፣ ነዋሪውን ለማሸበር መሞከራቸውም ታውቋል፡፡ በጎንደር አንዳንድ አካባቢዎች በነበረው የበዓል ስነ-ስርዓት ላይ በመንግስት ወታደሮች አስጀማሪነት በተፈጠረው ሁከት፣ በርከት ያሉ ወጣቶች ለእስር መዳረጋቸውን መረጃዎች ጠቁመዋል

በአፈሳ መልክ ታስረው የተወሰዱ ሰዎች ኢሰብዓዊ በሆነ የእስር ቤት አያያዝ ስር መውደቃቸውን የገለጹት የመረጃ ምንጮች፣ ታሳሪዎቹ የሚወሰድባቸው እርምጃም ከበድ የሚል እንደሆነ መረጃዎቹ አክለው ገልጸዋል፡፡ በቁጥጥር ስር የዋሉት ወጣቶችን አፋር ክልል የሚገኙ የበረሃ እስር ቤቶች በመውሰድ ከባድ ቅጣት እንደሚያደርሱባቸው የገለጹት ምንጮች፣ በተወሰደባቸው እርምጃ ህይወታቸውን ያጡ ወጣቶች መኖራቸውንም ምንጮቹ ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ልጆቻቸውን ፍለጋ ወደ ፖሊስ ጣብያ ያመሩ ወላጆችም ለጊዜው ልጆቻቸውን ማግኘት እንደማይችሉ ተነግሯቸው መመለሳቸው ታውቋል፡፡


ታፍሰው የተወሰዱ ወጣቶች በተለያዩ ማሰልጠኛ ካምፖች ትምህርት እየተሰጣቸው መሆኑን የሚገልጹት የመንግስት ኃላፊዎች፣ በታሳሪ ወጣቶች ላይ እየደረሰ ያለውን መከራ ዓይን ባወጣ ቅጥፈት ለማስተባበል ሞክረዋል፡፡ ከተያዙት ወጣቶች መካከል 99 ፐርሰንቶቹ የጸባይ ማረሚያ ዓይነት ትምህርት ወስደው እንደሚፈቱ የመንግስት ኃላፊዎች ቢገልጹም፣ ምንጮች ግን የታሳሪዎቹ ህይወት ከባድ አደጋ ላይ መሆኑን ነው የገለጹት፡፡

http://www.satenaw.com/amharic/archives/22108

No comments:

Post a Comment