Sunday, January 19, 2014

ክህደት ከአናት ሲጀምር:- በቀድሞው የኢትዮጵያ አየር ኃይል ውስጥ


እውነት ቤት ሥትሰራ
ውሸት ላግዝ ካለች
ሚስማር ካቀበለች
ጭቃ ካራገጠች
ቤቱም አልተሰራእውነትም አልኖረች
እንደዚያ ነው በባቢሎን ዘመን
የአንዱ ቋንቋ ከአንደኛው ይዘበራረቃል ….. መግባባትና መረዳዳት ብርቅ ይሆናል በጠራ አማርኛ የተጣፈውን በጉግማንጉግኛ በመተርጐም ከውስጡ የሚፈልጉትን ብቻ አለፍ አለፍ እያሉ ያነቡታል እናም የራሳቸውን ትርጉም ይሰጡታል ፍየል ወድያ ….. ቅዝምዝምም ወዲህ ይሆናል
ከቀድሞው የኢትዮጵያ አየር ኃይል አባላት መካከል ጥቂት አዛውንቶች ታሪክን ደልዘው በወያኒኛ አዲስ ታሪክ ስለ አየር ኃይሉ እንዲፅፉ በህውሃት እየተጠየቁ ነው እነዚህ ባለ ብዙ አኩሪ ታሪክ ባለቤት አዛውንቶች መንታ መንገድ ላይ ቆመዋል በዓለም ዙርያ ተበትነው ያሉት የቀድሞው አየር ኃይል አባላት ሃሳባቸውን እንዲደግፉና የእርዳታ እጃቸውንም እንዲዘረጉ ለማግባባት እየሞከሩ ነው እኛም የቀድሞው የአየር ኃይል አባላት እንዲህ አልን ……….

የአየር ኃይልን ታሪክ ለትውልድ ለማስቀረት የምታደርጉት ጥረት በጐና የሚደገፍ ምግባር ነው በርቱ ነገር ግን የገዢው ፓርቲ ሞግዚትነት አያስፈልጋችሁም በተጨማሪም በተፅዕኖ ስር ሆናችሁ ሚዛናዊነት የሚጐድለውና የተደለዘ ታሪክ ለትውልድ እንዳታቆዩ ሥጋት ቢጤ አለችን
(
ያም ቢሆን መፅሃፉን ካነበብን በኋላ የምንታዘበው ይሆናልአያጣላም ) የአየር ኃይል ቬተራን አሶሴሽንን እናቋቁማለን የምትሉትን በተመለከተ ግን ወራጅ አለ እጅግ ከስጋት በላይ የሆኑ ጥያቄዎች አሉን የቀድሞው አየር ኃይል ቬተራን አሶሴሽንእያላችሁን ከሆነ ግን እንግባባለን
የሚለውን ጥቅል ሃሳብ በመልዕክታችን ብንሰድላቸው በጉግማንጉግኛ በመተርጐም እኛ ፖለቲካ አንነካካም …. ፖለቲካንና ኰረንቲን በሩቁ ነው ብለናል ይሉናል ከአዲስ አባ ደብዳቤ እየፃፉ እነሱ ለካ የአሁኑን የህውሃትን መንደርተኛ አየር ኃይል ነው ቬተራን እያሉ የሚያንቆለጳጵሱት በህውሃት ሰማይ ስር ጉድ ሳይሰማ አያድርም አይደል !
እኛ ድፍን የአየር ኃይል ተቋም ላይ ስለተፈፀመ ክህደት ስናወራ …. እነሱ አንድ ግለሰብ አገርንና ህዝብን ለከዳ ስርዓት ስለሚመሰርተው ዕድርና የተዝካር ግርግር ሊያስረዱን ይሞክራሉ እኛ እኰ የቆማችሁበት አፈር ሥር ነፍሱ ያልወጣች የምታጣጥር የገዛ ጓደኛችሁ ነፍስ አለች ነው የምንላቸው
መጀመሪያ ባለንጀራችሁን ነፃ አውጡት እናንተም በጐን በሾርኔ ሳይሆን በአደባባይ በህግ ነፃ ውጡ ምክንያቱም እንደ ዶሮዋ ገመዳችሁ ረዘመላችሁ እንጂ ፈፅሞ አልተለቀቃችሁም እያልን ነው
ህውሃት እንደሆነ በሰው ተጠቅሞና አዋርዶ እንደሚያባርር የአደባባይ ሚስጢር ነው ደግሞም ይህ ይጠፋችኋል ብለን አንሞግትም ….. የመሰንበት ጉጉት ህሊናን ፈፅሞ ካልተቆጣጠረ በቀር አየር ኃይል ለአገር አንድነት የተፋለመ ጀግና እንጂ ጨፍጫፊ ያለመሆኑን በአደባባይ ስትመሰክሩና በህግ
ስታስነግሩ ….. የአየር ኃይል ተቋም እንደ ተቋም ነፃ ሲወጣ …. እርቅ ሲወርድ አገርን ከጠላት በመከላከላቸው ብቻ የሞትና የእድሜ ልክ ፍርደኞች በአደባባይ ነፃ ሲወጡ …. ያን ጊዜ ሁላችንም በአንድነት ነፃ እንወጣለን ያለበለዚያ ግን ትውልድም አገርም ላይ ይቅር የማይባል ክህደት ትፈፅማላችሁ እያልን ነው ያለነው በጠራ አገርኛ ቋንቋ
የቬተራን አሶሴሽንን በመወከል ያገባኛል ብለው ከአዲስ አበባ መልዕክት የሰደዱልን ሰው በፍፁም ሃሳባችንና ሥጋታችንን በትክክል የተገነዘቡ አይመስሉም ወይንም ዛሬ ኢትዮጵያ በምትባለው አገር ውስጥ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ የሚከታተሉም መሆናቸውን እንድንጠራጠር እያደረገን ነው ድንገት ዘንድሮ ጆሮዋቸውም ዓይናቸውም የተከፈተላቸው ይመስል በቃል ያጠኑትንና ስለ አየር ኃይሉ የሚገምቱትን በጐ ፍላጐት ለመተግበር የተነሱ ይመስላል
የህውሃት አስተዳደር አዛውንት የአየር ኃይሉን አባላት በማምሻ እድሜያቸው ታሪክን ደልዘው የእራሱን የተንጋደደና የተንሸዋረረ ታሪክ እንዲፅፉለት እየተጠቀመባቸውና ከጠራ ታሪካቸው አንስቶ ከራሱ ቆሻሻና ስውር ፍላጐት ሥር እያንደባልላቸው ያለ ይመስላል አየር ኃይሉ በአዋጅ ሙሉ ለሙሉ ከስራ ውጪ በተደረገበት ዘመን ላይ ጨፍጫፊ ተብሎም ቅፅል ስም ወጥቶለት ወደ ከርቸሌ መጋዙንና በመንደርተኛ ፓይለቶች እየተተካ መሆነኑን ትንፍሽ እንዳይሉ በዚሁ በምሽት እድሜያቸው እየተደለሉ ናቸው እንዲያውም ሙዝየም እስከ መክፈት የዘለቀ ህልምም እንዳላቸው እየጠቀሱ ነው አገር ቢኖረንማ ኖሮ ለትውልድ የሚቀር ታሪክን የሚዘክር ሙዝየም ማቆም እንዴት የተባረከ ህልም ነበር ? ነገር ግን አገርም ዜግነትም በተዋረዱበትና እድሜያቸውን ሙሉ ለአገር አገልግሎት ያበረከቱ አንጋፎች እንደ አሮጌ ቁና በውርደት እንዲኖሩ በአደባባይና በአዋጅ ባይበየን ኖሮ ትውልድም በበጐ መሰረት ላይ ቀጥሎ ቢሆን ኖሮ …. ሁሉም አላማ በጐና ለአገርም ሆነ ለትውልድ የሚጠቅሙ ይሆኑ ነበር
እንግዲያውስ እነዚህ በህውሃት እየተደለሉ ያሉት የአየር ኃይሉ ነባር አዛውንቶች እርማቸውን ያውጡ ህውሃት አገሪቷን ከተቆጣጠረ ወዲህ ያለውን አየር ኃይል ተብዬ እንጂ የቀድሞውን ታሪክ ምናምኒት አሻራ እንኳ አያገኙም አጠቃላይ ሰፈሩና ቢሮዎቹም ጭምር በአይጥ መንጋ እንደተመታ ባድማ ዶክመንቶች ተፈርፍረው ድምጥማጣቸው መጥፋቱን አይጠራጠሩ የአየር ኃይሉን የታሪክ አሻራ ሊያስረዱ የሚችሉ የተለያዩ አውሮፕላኖችን ማናምኒት ሳያስቀር አቧራቸውን እያራገፈ የህውሃቱ አበበ /ኃይማኖት (ጆቤ) እዚህ ግባ በማይባል ዋጋ መቸብቸቡን እንዴት ሳይነግራቸው እንደቀረ ይገርመናል ? ይህ ቀበኛ ሽፍታ ለጌጥና ለታሪክ በአየር ኃይሉ /መምሪያ ፊት ለፊት እንኳ ተቀምጣ የነበረችውን ገብሬ ቦላሌን ሳይቀር አንጠፍጥፎ መሸጡን ለምን ደበቃቸው ? ታሪክ በመስራት አገራችንን ያስከበረችውን ኤፍ-5 አውሮፕላንንስ አንዲት ሳያስቀር መቸብቸቡንስ ?
በትግራይ ነፃ አውጪ ግንባር የሚመራውን የአሁኑን ሥርዓት አያውቁትም እንበል ወይስ የክፋትና የብቀላ ምግባሩን ሁሉ ትተው በጐ ተክለ ሰውነት ሊገነቡለት እየሞከሩ ይሆን ? ታዲያ ይህንን እየሰሩ እንዴት ፖለቲካ አንነካካም ይሉናል ? በእነርሱው አመራር ስር የተገነባው የአየር ኃይል ሰራዊት እኰ በጅምላ ጨፍጫፊና ወንጀለኛ ተብሎ እድሜውን ሙሉ ከአቀናው መስሪያ ቤት በውርደት ተባሮ ቤተሰቡ ተበትኖ በረሃብና በችጋር እንዲያልቅ ተፈርዶበታል ! እውነተኛዎቹ የአየር ኃይሉ አርበኞች ድፍን 22 ዓመታት ሙሉ ተሸማቀውና አንገታቸውን ደፍተው መሃል / ውስጥ (በቀለ ሞላ ሆቴል ፊት ለፊት) በጠጠርና በቆርኪ ዳማና ቼዝ ሲጫወቱ የአዛውንቶቻችን መንግስት የት ነበር ? ለዚህ ሁሉ ግፍና በደል ተጠያቂው ማነው ? እነዚህንና ሌሎች በደሎችን እንዴት ነው የሚያስታርቁት ? በምንስ መመዘኛ ቀበኛ ሽፍታ የመሰረት ድንጋይ እንዲያነጥፍላቸው ያደርጋሉ …. ! ከረገጡት ምድር ስር
የባልንጀሮቻቸው የምትቃትት ነፍስ ምን ትላቸው ይሆን ? ፖለቲካፖለቲካ …. ለምን እንደሚሉን አልገባንም ፖለቲካ ምንድነው ?
ለዘመነኖቹ የመንግስት ባለስልጣናት ማደር ? ለስብሰባ ሲጠሩ ፈጥኖ ሸገር ላይ መከሰት ? ወይስ ሲመሩት የነበረውን ሰራዊት አስማርኰና ክዶ ለትግራዩ የነፃነት (ተገንጣይ) ግንባር በፈቃደኝነት መገበር ? እኛ ፖለቲከኞች እያሉን የሚያበሻቅጡን ከአገር በግፍ ተገፍታሪ ስደተኞች በሰላም ተከባብረንና ተዛዝነን ድፍን 20 ዓመታትን እንዳሳለፍን በአለፈው የበጋ ወቅት በዋሽንግተን ከተማ ተገኝተው መታዘባቸውን እናውቃለን አየር ኃይል ማለት ለኛ መታወቂያችን ማንነታችንና ዜግነታችንም ጭምር ነው በህብረት ተደጋግፈን እንኖራለን የተቸገረን እንረዳለን የታመመን እናስታምማለንእንጠይቃለን እስከወዲያኛው የሚሰናበተንንም በኃዘን እንሸኛለን
ጀግኖቻችንን ከተጣሉበት እያስታወስንና እያነሳን እናከብራቹኋለን እንላለን በየዓመቱም የአየር ኃይል ቀን በማለት በህብረት ዩኒፎርማችንን ለብሰን ባንዲራችንን ከፍ አድርገን እያውለበለብን ኢትዮጵያ ሃገሬን እንዘምራለን ….. ይህንን ባንዲራና ዝማሬ የአሁኑ መንግስት አይወደውም በዘር ከፋፍሎ እኛ እና እነርሱ የቀድሞውና የአሁኑ ጨፍጫፊና ዲሞክራቲክ በማለት እየለያየ አጥፍቶናል አሁን ደግሞ እዚሁ ያለንበት አገር ድረስ ክንዱን እያረዘመ መካከላችን ሊገባ እየተቅበዘበዘ እንደሆነ ይገባናል እባካችሁን አዛውንቶቻችን ለዚህ መንደርተኛ ስርዓት ክርንና ጅማት እየሆናችሁ ህውሃት ጣቱን እቤታችን ድረስ እንዲያረዝም እየረዳችሁ መካከላችን እንዲገባ አታድርጉ በማህበራችንም በኩል አትምጡ
በግል እኰ መፅሃፍ አይደለም ኤግዚቢሽንም መክፈት ትችላላችሁ አሁን እየመጣችሁበት ያለው መንገድ ግን የሁሉንም ምክር የብዙሃንን ይሁኝታ ይጠይቃል እናንተ ደግሞ እዚያው አገር ቤት ያሉትን እውነተኞቹን አርበኞች አንድ በአንድ ሲያልቁ ጠብቃችሁ በህይወት የተረፉትንም ንቃችሁና ገፍትራችሁ ቀበኛ የሃገር ጠላት የሆኑትን ቱባ የህውሃት ባለስልጣናትን በጀርባችሁ አዝለችሁ አትላንቲክን በማቆራረጥ ልታነታርኩን ትሞክራላችሁ። ለምን ድምፃችሁን አጥፍታችሁ ታሪክ መፃፍም ሆነ ዕድር ማቋቋም አልመረጣችሁም ? በማህበራችን በኩል ለመምጣት ለምን መረጣችሁ …. ? በብዙሃን ስደተኛና በውርደት ተባራሪ ስም በየሸራተኑ ከበሮ መደለቁንስ ምን አመጣው ?
እንግዲያውስ ለሁለተኛ ጊዜ ምክር እንለግስ ……….
ሰው ባለቀ እድሜው ላይ ለኑዛዜ ይመቻቻል ….. እውነትን ተናግሬ ካልሞትኩ ብሎ ከህሊናው ጋር ትንቅንቅና እልክ ይጋባል ….. እውነቱን አፍርጦ በመሸበት ያድራልእንጂ ለዳግም ምርኰ እራሱን አሳልፎ አይሰጥም በዚህ እድሜ እኰ ግጥም ብሎ ከሞላ የውስኪ ባንኰኒ ላይ የምንጭ ውሃ ካልሆነ ንክች አላደርግም .. ከተትረፈረፈ ጮማና ቁርጥ መሃል ቲማቲምና ቅጠላ ቅጠል ካልሆነ ምናምኒት አልቀምስም እየተባለ የሚኖርበት እድሜ ነው ብዙ የሚያጓጓ ህይወት የለም ታዲያ ምንድነው በዚህ በኪኒኒ ተደግፎ በሚኬድበት የምሽት እድሜ ላይ ሆኖ ውሃና ዘይትን ለመቀላቀል መሞከር ? በዚህ ምግባር ትውልድ አይደለም ከአብራክህ የወጣ ልጅ ይጠየፍሃል
እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይባርክ
ታዛቢዎች በህብረት !
ከቀድሞው የኢትዮጵያ አየር ኃይል በያሉበት


https://www.zehabesha.com/amharic/archives/12019

No comments:

Post a Comment