Tuesday, February 11, 2014

ባለ532 ብር ደመወዝተኛው የሕወሓት ታጋይ ከ10 ሚሊዮን ብር ያላነሰ ሃብት ማግበስበሱ ተሰማ

(ኢሳት ዜና) የደህንነት ሃላፊ ከነበሩት ከአቶ ወልደስላሴ ወልደ ሚካኤል ጋር በግብረ-አበርነት የተከሰሱት የህወሃት ታጋዮች ከደሞዛቸው ጋር ፈጽሞ የማይመጣጠን ሃብት አግበሰው መገኘታቸው ታውቋል።

በተለያዩ አለመግባባቶች የተነሳ እየተመሰረቱ ያሉ ክሶች የህወሃት ተጋዮች በህገወጥ መንገድ የሰበሰቡትን የሃብት መጠን ለማወቅ እየረዳ መሆኑን የገለጸው ዘጋቢያችን ከአቶ ወልደስላሴ ጋር በግብረ አበርነት የተከሰሱት የህወሃት ታጋዩ የአቶ ወልደስላሴ ወንድም አቶ ዘርአይ ወልደስላሴ የመከላከያ ሚኒስቴርን ሲለቁ በመጨረሻ ይከፈላቸው የነበረው ወርሃዊ ደሞዝ 532 ብር ብቻ እንደነበር አመልክቷል ፡፡ ይሁንና፣ ጸረ-ሙስና ኮሚሽን ባደረገው ማጣራት ግለሰቡ በተለያዩ ባንኮች በስማቸው 5 ሚሊዮን ብር ከማስቀመጣቸውም በተጨማሪ፣ አዲስ አበባ ቤቴል ሆስፒታል አካባቢ 74 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ግንባታ እያካሄዱ በአፋር ክልል ደግሞ 1 ሚሊዮን 400 መቶ ብር በላይ በሆነ ወጪ የእርሻ ኢንቨስትምንት እያከናወኑ መሆናቸው እንዲሁም በስማቸው 2 ሚሊዮን 700 ብር ግምት ያላቸው 2 ሎደር መኪኖች መገኘታቸውን ገልጽዋል።
የአቶ ወልደስላሴ እህት የሆኑት / ትርሃስ ደግሞ 8 ክፍል ተማሪና ምንም ስራ ያልበራቸው ሲሆን፣ በወንድሞቻቸው ድጋፍ 2 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገዛ አንድ ስካቫተር፣መኪና እንዲሁም በአዲስ አበባ በየካና ቦሌ ክፍለ ከተሞች፣ በለገጣፎ፣ መቀሌና አክሱም 3 266 ካሬ ሜትር ቦታዎች በስማቸው መገኘቱ ተመልክታል ፣እንዲሁም በተለያዩ ባንኮችም 8 ሚሊዮን ብር ተቀማጭ ማድረጋቸውን አንድ ተጨማሪ ዘመናዊ መኪና በስማቸው ተመዝግቦ መገኘቱን ጸረ ሙስና ኮሚሽን በምርመራ አረጋግጧል።
ዋናው ባለስልጣን አቶ ወልደስላሴ ደግሞ ስራ ሲጀምሩ ደሞዛቸው 1600 ብር የነበረ እና በእድገት እስከ 6000 ብር ሲከፈላቸው የቆየ ቢሆንም ያካባቱት ሀብት ግን ፈጽሞ ከደሞዛቸው ጋር የማይመጣጠን ነው ተብሏል። ባለ 4 ፎቅ ህንጻ ባለቤት የሆኑት አቶ ወልደስላሴ 1 አመት 2 ወራት ቤቱን አከራይተው 790 ብር ገቢ አግኝተዋል።
አቃቢ ህግ ያቀረበውን ክስ የእስረኞች ጠበቆች፣ አዲስ የተጨመረ ክስ ነው በማለት አቤቱታ አቅርበዋል።
አቶ ወልደስላሴ ከወ/ አዜብ ጋር በነበራቸው መቀራረብ ከፍተኛ ሃብት ማፍራታቸውን አቶ መለስ ዜናዊ ከሞቱ በሁዋላ ግን የእርሳቸው ዋነኛ ተቀናቃኝ የሆኑት የደህንነቱ ዋና አዛዥ አቶ ጌታቸው አሰፋ ግለሰቡን በሙስና ከሰው እንዳሳሰሩዋቸው አንዳንድ የመገናኛ ብዙሀን ገልጸው ሲዘግቡ ቆይተዋል።
ህወሃቶች እርስ በርስ በሚያደርጉት ሽኩቻ እየተካሰሱ ፍርድ ቤት መቅረባቸው የካበቱትን ሃብት ለማወቅ እየረዳ ነው የሚለው ዘጋቢያችን፣ በጸረ ሙስና ኮሚሽን ያልተመረመረና በፍርድ ቤት ቀርቦ ያልታወቀ ከዚህም የባሰ የሙስና ታሪክ እንደሚኖር መገመት ይቻላል ሲል አስተያየቱን አስፍሯል።


ምንጭ፡ ኢሳት ቲቪ

   https://www.zehabesha.com/amharic/archives/12729

No comments:

Post a Comment