Saturday, February 1, 2014

ድንበሩ፤ ጎንደር – መተማ

መቼ መሰላችሁ 1999 ሚሊኒየሙ እንደ ነገ ሊጠባ እንደ ዛሬ በሉት እኔ እና ጓደኞቼ ወደ መተማ ለአንድ ስራ ተጉዘን ነበር፡፡ በነገራችን ላይ፤ ወደ መተማ ስትሄዱ ጭልጋ ላይ ከደረሳችሁ በኋላ በጣም ብትንደረደሩ መተማን አልፋችሁ ሱዳን ጋላባት የመግባት እድላችሁ የሰፋ ነው፡፡ የሱዳኗ ጋላባት እና የእኛቱ መተማ ማለት አፍንጫ እና አፍ እንደማለት ናቸው፤ አረ አፍንጫ እና አፍ በጣም ይራራቃሉእኛም እዛ ለመድረሳችን ማስረጃ እንዲሆነን ሱዳኗ ጋላባት ገበያ ሸበጥ ጫማ ገዝተን ነበር፡፡
በዛ ጉዞ ከነበረን ትዝታ ውስጥ ፈፅሞ የማይረሳን አርበኞች ግንባር ፈፀማቸው የሚባሉት ጀብዱዎች እና የአካባቢው ህዝብ ለግንባሩ የነበረው አድናቆት እና ፍቅር ነበር፡፡ ቦታው አርበኞች ግንባር አባላት ሲመቻቸው መሳሪቸውን ሳይመቻቸው ደግሞ ቀበቷቸውን ታጥቀው የሚንጎማለሉባት ስርፋ ነበረች፡፡
በአካባቢው ከሱዳን ጋር ስላለን ድንበር ጉዳይ ከመተማ ወደ ውስጥ ገብተው ያሚገኙ ገበሬዎች ጥቂት ጥቂት አጫውተውኛል፡፡
በሱዳን እና በኢትዮጵያ መካከል ያለው ድንበር ሰፊ አውላላ ሜዳ ነው፡፡ ባለፈው ጊዜ ፕሮፌሰር መስፍን ሲናገሩ እንደሰማነው ሁለት አይነት ድንበር አለ አንደኛው መንግስት የሚያውቀው ሌላኛው ደግሞ ህዝቡ የሚያውቀው ነው፤ እንደ ፕሮፍ አባባልህዝቡ ይሄ ነው ሀገሬ የሚለው እና መንግስት ይሄ ነው ካርታዬ የሚለው አንዳንዴ ይለያያል አንዳንዴ ደግሞ ይመሳሰላል፡፡
የአካባቢው ገበሬዎች ስለ ድንበሩ አካባቢ ሲያወሩ አካባቢው ለዘመናት ሲጋደሉበት የነበረ አካባቢ ነው፡፡ ብዙ ጊዜ የመጋደሉ መነሾ ጎንደሮች የዘሩትን የሱዳን አርብቶ አደሮች በከብት ሲያሳጭዱት በሚነሳ ግጭት መሆኑን ስሙን የዘነጋሁት ገበሬ አውግቶኝ ነበር፡፡ ገበሬው እንደነገረኝ አካባቢው ላይ ሱዳኖችም የእኛ እኛም የእኛ የምንለው ሰፊ መሬት አለ እኛ እህል እንዘራበታለን እንርሱ ደግሞ ከብት ይዘሩበታል፡፡ በዚህም የተነሳ የሀገሬ ገበሬ እና የጎረቤታችን አርብቶ አደር ማዶ ለማዶ ሆነው ይታኮሳሉ፤ ይጋደላሉም፡፡
ባለፈው ጊዜ አንድ የሱዳን ድረ ገፅ ጽፎት አንዱ ወዳጄ ደግሞ አጋርቶን እንዳየሁት ሱዳኖች ከኢትዮጵያ ጋር የድንበር ግጭት ደጋግሞ ሲከሰት የነበረበት አካባቢ ችግር መፈታቱን ጽፈዋል፡፡ አክለውም በአካባቢው ላይ መንግስታቸው ወደ አስራ ሰባት መንደሮችን ሊያሰፍር እቅድ መያዙን አውርተዋል፡፡
ማን መሬት ላይ ማን ይሰፍራልይሄ በውል አለየም፡፡ ሰዳኖች የገዛ መሬታቸው ላይ ነው ይሄንን መንደርተና ሊያሰፍሩ ያቀዱት ወይስ የገዛ አውላላ ሜዳቸውን ሊስጠብቁ ነው… (ትላንት ስለ ፕሮፍ ስናወራ ያነሳነውም ይሄንኑ ነው)
የሀገሬ ሰዎች መሬታቸው ላይ እንኳንስ መንደር መስርተውባቸው ይቅርና ሳሬ ላይ ከብት ተለቀቀ ብለው የሚታኮሱ ናቸው፡፡ መንግስታችን በአካባቢው ላይ ያለውን እንደ አርበኞች ግንባር የመሳሰሉ ታጣቂዎችን ለመቆጣጠር ሲል መሬቱን ለሱዳኖችእንሆ በረከትሊል አይችልም ብሎ የሚከራከር ካለ እርሱ ኢህአዴግ መስተፋቅር ያሰራችበት ምስኪን አፍቃሪዋ ብቻ ነው፡፡ እንደዛም ሆኖ ግን መንግስት አይምሮውን ጨለፍ አድርጎት መሬቱን ለመስጠት ሲስማማ የአካባቢው ገበሬዎች የሚያስቀምሱ ናቸው ብሎ ማሰብም ከባድ ነው፡፡
ትልቁ ቁምነገር መንግስት እንዲህ አይነት ትልልቅ ጉዳዮች ላይ ውሳኔ ሲያደርግ ለህዝቡ ግልጽ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ገንዘብ ሲቸገር ብቻ ቦንድ ግዙልኝ ብሎ ወደ ህዝቡ መምጣት ከመንግስትነት ወደ የኔብጤነት ዝቅ የሚደርግ አሰራር ነው!
በነገራችን ላይ ለነገ ጎንደር ላይ በሰማያዊ ፓርቲ የተጠራው ሰልፍ መልእክትም ይሄው ነው፡፡ መንግስት ከጎረቤት ሀገራት ጋር በመንሾካሾክ መስራቱን ያቁምግልጽነት እና ተጠያቂነት ያለበት አስራር ይስፈን!

 http://www.zehabesha.com/amharic/archives/12407

No comments:

Post a Comment