Wednesday, June 10, 2015

የሽብርተኝነት ክስ በተመሠረተባቸው የፓርቲ አመራሮችና ግለሰቦች ላይ ምስክርነት መስማት ተጀመረ

በሽብርተኝነት ተጠርጥረው ክስ የተመሠረተባቸው የቀድሞ የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ (አንድነት)፣ የአረናና ሰማያዊ ፓርቲዎች አመራሮች ላይ፣ ዓቃቤ ሕግ ምስክሮቹን ከሰኔ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ማሰማት ጀመረ፡፡

ክሱን የመሠረተው የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ምስክሮቹን አቅርቦ ከማሰማቱ በፊት፣ በፀረ ሽብርተኝነት አዋጁ አንቀጽ 32 መሠረት ምስክርነቱ በዝግ እንዲታይ ለፍርድ ቤቱ አመልክቷል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ‹‹በምስክሮቼ ላይ ማስፈራሪያና ዛቻ ደርሶባቸዋል›› የሚል ነበር፡፡

ተከሳሾቹ ግን የተጠቀሰባቸው ሕግ እስከ ሞት ድረስ ሊያስቀጣ የሚችል መሆኑን በመጠቆምና ምስክርነቱን ሕዝብ መስማት እንዳለበት በመግለጽ፣ ምስክርነቱ በግልጽ ችሎት እንዲታይ ፍርድ ቤቱን በመጠየቅ የዓቃቤ ሕግን ማመልከቻ ተቃውመዋል፡፡

ሁሉንም እስረኞች በመወከል ለፍርድ ቤቱ ያመለከቱት የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ አመራር አቶ ሀብታሙ አያሌው ሲሆኑ፣ ያሉት ማረሚያ ቤት ውስጥ መሆኑንና የምስክሮቹ ዝርዝር ሊደርሳቸው የሚገባ ቢሆንም መከልከላቸውን አስረድተዋል፡፡

በመሆኑም በምስክሮቹ ላይ ማንም ዛቻና ማስፈራሪያ ሊያደርስ የሚችልበት መንገድ እንደሌለ ጠቁመው፣ የዓቃቤ ሕግ ጥያቄ ውድቅ እንዲደረግላቸው አመልክተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ምስክርነቱን በዝግ ችሎት የሚያየው ከሆነ፣ ሁሉም ተከሳሾች የግፍ ፍርደኛ ሆነው ወደ እስር ቤት እንደሚመለሱና በቀጣይም ምንም ዓይነት ክርክር እንደማያደርጉ ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የሁለቱንም ወገኖች ክርክር በማዳመጥ ውይይት ካደረገ በኋላ፣ የዓቃቤ ሕግን ማመልከቻ ውድቅ በማድረግ፣ ምስክርነቱ በግልጽ ችሎት እንዲታይ ብይን ሰጥቷል፡፡ ነገር ግን የዓቃቤ ሕግ ምስክሮች የሚናገሩትንም ሆነ ስማቸውን ጠቅሰው የኅትመትም ሆነ የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙኃን መዘገብ እንደማይችሉ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

በዕለቱ በአሥረኛ ተከሳሽ አቶ ተስፋዬ ተፈሪ ላይ አንድ የዓቃቤ ሕግ ምስክር ተሰምተዋል፡፡


ተከሳሾቹ አቶ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ጋሻው፣ የአንድነት አመራር የነበሩት አቶ ሀብታሙ አያሌውና አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ የአረና ፓርቲ አመራር አቶ አብርሃ ደስታ፣ እንዲሁም አቶ ዮናታን ወልዴ፣ አቶ አብርሃም ሰለሞን፣ አቶ ሰለሞን ግርማ፣ አቶ ባህሩ ደጉና አቶ ተስፋዬ ተፈሪ መሆናቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/44193

No comments:

Post a Comment