Friday, June 19, 2015

‹‹በምርጫው ምክንያት ሊበቀሉን ነው ቤታችን በክረምት ያፈረሱት›› ኢህአዴግን አልመረጣችሁም በሚል የለገጣፎ ነዋሪዎች ቤታቸው እንደፈረሰባቸው ገለጹ

በ2007 ዓ.ም ሀገራዊ ምርጫ ኢህአዴግን አልመረጣችሁም በሚል ቤታቸው እንደፈረሰባቸው በለገጣፎ አባኪሮስ፣ ገዋሳ አካባቢ ነዋሪዎች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ነዋሪዎቹ በተለያዩ ጊዜያት ፖሊስና ካድሬዎች ቤታቸውን በቀይ ቀለም ከቀቡ በኋላ በተደጋጋሚ ገንዘብ ሲቀበሏቸው እንደቆዩና ከሰኔ 09/2007 ዓ.ም ጀምሮ በምርጫው ሰበብ ቤታቸውን እያፈረሱ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የአካባቢው ህዝብ ‹‹ቤትክን እናፈርሳለን!›› እየተባለ በደተጋጋሚ በሚከፍለው ሙስና የተማረረው እንደሆነ የገለጹት ነዋሪዎቹ በአካባቢው ኢህአዴግ እንዳልተመረጠ ገልጸዋል፡፡ ይህን ተከትሎም ኢህአዴግን ያልመረጡ በተለይም ሰማያዊ ፓርቲን መርጠዋል የተባሉ ነዋሪዎች ቤት ቀይ ምልክት ተቀብቶ እንዲፈርስ መደረጉን ገልጸዋል፡፡ ከምርጫው ጋር በተያያዘ ቤታቸው እንዲፈርስ ቀይ ምልክት ከተቀባባቸው መካከል ለፖሊስና ካድሬዎች ጠቀም ያሉ ገንዘብ የከፈሉ ነዋሪዎች እንዳይፈርስባቸው ሲደረግ ገንዘብ መክፈል ያልቻልነው ቤታችን ፈርሶብናል ብለዋል፡፡

ነገረ ኢትዮጵያ ቢሮ ድረስ በመምጣት መረጃውን ያቀበሉን ነዋሪዎቹ ‹‹ኢህአዴግን አልመረጣችሁም፣ ሰማያዊ ፓርቲን ነው የመረጣችሁት በሚል ቤታችን ፈርሶ በአሁኑ ወቅት ከእነ ልጆቻችን ጎዳና ላይ ወድቀናል፡፡›› ብለዋል፡፡ ‹‹እስካሁን ቤታችሁን እናፈርስባችኋለን ብለው በማስፈራራት ከፍተኛ ገንዘብ ሲያስከፍሉን ቆይተዋል፡፡ ቆርቆሮ ገንጥለው ለቆርቆሮው እስከ 2 ሺህ ብር አስከፍለው እንደገና ቆርቆሮውን ይመልሱልን ነበር፡፡ አሁን ደግሞ በምርጫው ምክንያት በአካባቢው ህዝብ ቂም ይዘዋል፡፡

 በምርጫው ምክንያት ሊበቀሉን ነው ቤታችን በክረምት ያፈረሱት›› ያለው አንድ ወጣት ሙስና ከፍለው ቤታቸው እንዳይፈርስ ካደረጉት ባሻገር እየዞሩ ቤት የሚያፈርሱት ፖሊሶችና ደህንነቶች በአካባቢው በርካታ ቤቶችን ማስገንባታቸውና የእነሱ ቤት እንደማይፈርስባቸው ገልጾአል፡፡ የካድሬዎች፣ የፖሊሶችና ገንዘብ የሚከፍሉት ሲቀር ‹‹ኢህአዴግን አልመረጣችሁም፡፡

 የመረጣችሁት ተቃዋሚዎችን በተለይም ሰማያዊ ፓርቲን ነው›› ተብለው ቤታቸው እንደሚፈርስ ተነግሯቸው ሙስና መክፈል ያልቻሉት ነዋሪዎች ቤት ተመርጦ እየፈረሰባቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ገዋሳ፣ ጪሚሲና ሚሽን የተባሉ አካባቢዎች ቤቶች እየፈረሱ መሆኑን የገለጹ በለገጣፎ የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩ የነበሩት አቶ አበበ አካሉ ‹‹የነዋሪዎች ቤት እየፈረሰ የሚገኘው በምርጫው ምክንያት ነው፡፡ ለገጣፎ አካባቢ ምርጫው መጭበርበሩን ያጋለጡ ሰዎች ከፍተኛ ጫና ደርሶባቸዋል፡፡ እኔ ጋርም እንዳይገናኙም ወከባ ይፈፀምባቸዋል፡፡ አሁን ደግሞ ህዝቡ ኢህአዴግን ባለመምረጡ ቤቱን እያፈረሱበት ነው፡፡›› ብለዋል፡፡

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/44486

No comments:

Post a Comment