Wednesday, September 9, 2015

ጦማሪያኑ ለአራተኛ ጊዜ ለብይን መቀጠራቸውን ተቃወሙ



‹‹አንድ ዳኛ ምንም ማድረግ አይችልም›› ዳኛ ዘሪሁን ደሳለኝ

‹‹ከዳኞች ጋር ምንም ችግር የለብንም ከማን ጋር እንደተጣላን ገብቶናል›› በእስር ላይ ያሉ ጦማሪያን

በተጠረጠሩበት የሽብር ተግባር ወንጀል ክስ ከተመሠረተባቸው በኋላ የከሳሽ ዓቃቤ ሕግ የሰውና የሰነድ ማስረጃ ቀርቦባቸው ለብይን የተቀጠሩት አራት ጦማሪያን፣ ለአራተኛ ጊዜ ጳጉሜን 2 ቀን 2007 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ መሰጠቱን ተቃወሙ፡፡

ተከሳሾቹ ጦማሪያን ናትናኤል ፈለቀ፣ አቤል ዋበላ፣ አጥናፍ ብርሃኔና በፍቃዱ ኃይሉ ጳጉሜን 2 ቀን 2007 ዓ.ም. ብይን እንደሚሰጥ የጠበቁ ቢሆንም፣ ጉዳያቸው በሦስት ዳኞች የሚታይ ከመሆኑ አንፃር በዕለቱ አንድ ዳኛ አቶ ዘሪሁን ደሳለኝ ብቻ የተገኙ በመሆናቸው ብይኑ ሳይሰጥ ቀርቷል፡፡ ብይኑ ተሠርቶ የተጠናቀቀ ቢሆንም፣ ዳኞች ባለመሟላታቸውና በመዝገቡ ላይ ባለመፈረማቸው ብይኑ ሊነገር እንደማይችል ዳኛ ዘሪሁን ገልጸዋል፡፡

በዳኞች አለመሟላት ለሁለተኛ ጊዜ መቀጠሩ ያበሳጫቸው ተከሳሾቹ፣ ‹‹እኛ ከዳኞች ጋር ምንም ችግር የለብንም፡፡ ከማን ጋር እንደተጣላን ገብቶናል፡፡ የምንፈልገው ቁርጥ ያለው እንዲነገረን ነው፡፡ ወይ በነፃ እንሰናበት ወይም ተከላከሉ እንባል፡፡ ብይን ለመስጠት በሚቀጠሩት ቀናት መካከል ያለው ጊዜ ለእኛ ሕመም ነው፤›› በማለት ቅሬታቸውን ተናግረዋል፡፡

የጦማሪያኑ ጠበቃ አቶ አመሀ መኰንን ‹‹ዳኞች እንዲሟሉ መተባበር ያለብን ነገር ካለ እንተባበር ወይም ለፍርድ ቤቱ አስተዳደር እናመልክት፤›› የሚል ሐሳብ ለዳኛ ዘሪሁን አቅርበዋል፡፡ ዳኛው በሰጡት ምላሽ፣ ‹‹የሚቻል ከሆነ ሞክሩ፤›› ብለዋል፡፡ እሳቸውም ብይኑ ቢሰጥ እንደሚመርጡ፣ ተጠርጣሪዎቹን ዓይናቸውን ባያዩ ደስ እንደሚላቸውና (በተደጋጋሚ በመመላለሳቸው) በግላቸው እንደሚከብዳቸው ተናግረዋል፡፡


ያልተሟሉት ዳኞች በተለያዩ ምክንያቶች መቅረታቸውን በመጠቆም፣ እንደተሟሉ እስከ መስከረም 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ድረስ ለማረሚያ ቤቱ ተነግሮ ብይኑ ሊሰጥ እንደሚችል በጽሕፈት ቤት አስታውቀዋል፡፡

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/46556

No comments:

Post a Comment