Friday, April 11, 2014

በባህር ዳር በተነሳ ግጭት ፖሊስ በጥይት ሕዝብ በድንጋይ ተከታከቱ፤ የሞቱም የቆሰሉም አሉ

(የባህር ዳር ከተማ ፎቶ ፋይል)

ለዘ-ሐበሻ ከባህዳር የደረሱ መረጃዎች እንዳመለከቱት ዛሬ በከተማዋ በፖሊስና በህብረተሰቡ መካከል በተደረገ የተኩስና የድንጋይ ውርውራ ልውውጥ ሰዎች ሞተዋል፤ የቆሰሉም አሉ፡፡ ፖሊስና ልዩ ሃይል በጥይት፤ ሕዝቡ በድንጋይ ባደረጉት መከታከት ከፖሊስም እንዲሁ የቆሰሉ እንዳሉ ተገልጿል፡፡

ዜናውን ያደረሱን የዘ-ሐበሻ ምንጮች እንደሚሉት ተኩሱ ለተከታታይ ሶስት ሰዓታት የተደረገ ሲሆን ህዝቡቤታችን ለአምስትና ስድስት ዓመታት ያህል ሰርተን እየኖርንበት ያለ እና ሌላ ተለዋጭ ቤት የሌለን በመሆኑ ወይ ተለዋጭ ቦታና ቤት ስጡን ወይም ደግሞ የትንሳኤን በዓል እንኳን እንዋል አታፍርሱብን፤ ሌላ መቀመጫ የለንምብሎ ሲጮህ ማፍረሱን ቀጥለው፤ በፖሊስ እና ሚሊሻ የታጀበው አፍራሽ ከህዝቡ ጋር ግጭት ጀምሮየተኩስ እሩምታ ህዝቡ ላይ መተኮስ በመጀመራቸው ህዝቡም ምላሽ በመስጠት ሲብሰውም ወንጭፍ በመጠቀም ሴቱም ወንዱም አንድ ላይ ሆነው ትንሽ ትልቅ ሳይል ተማምለው በመውጣት ከፖሊስ ጋር ፖሊስ በጥይት ህዝቡም በድንጋይና ባገኘው ሁሉ ተኩስ ሲለዋወጡ ለሶስት ሰዓታት ቆይተዋል፡፡

እንደ መረጃዎቹ ገለጻ በርካቶች ቆስለዋል ከፖሊስም ከህዝቡም፡፡ በኋላም ፖሊስ ህዝቡን ሲያባርር ህዝቡ እደገና ፖሊስን ሲያባርር ከቆዩ በኋላ ህዝብ ፖሊሱን ሁሉ እያባረረ ወደ መሃል ከተማው ቀበሌ አስራ ሶስት ጎፋ አካባቢ ሲደርሱ የመጣው ልዩ ሃይል ህዝቡ ላይ አስለቃሽ ጭስ በመጠቀም ለመበተን ቢሞክሩም ሳይችሉ ቀርተው ህዝቡ በአንድ ሆሆሆ ብሎ በመሄድ ልዩ ሃይሎችንም በድንጋይና ጠርሙስ መቀጥቀጥ ይጀምራል፡፡

በዚህ ሰዓት የሞቱና የቆሰሉ በርካታ ናቸው ለጊዜው ቁጥራቸው አልደረሰንም፤ ከባህርዳር ያለው ምንጫችን ሲልክልን ለህዝብ እናደርሳለን፡፡ ፖሊስም ግሬደር በመያዝ ችግሩ ወደተፈጠረበት አካባቢ በመሄድ አያሌው ጎበዜ የሚባለውን ሰፈር እስከ ቤት እቃዎቻቸው ድረስ ጠራርጎ በማፈራረስ እና በአካባቢው የሚንቀሳቀስን ወጣት በሙሉ ለቃቅመው በማሰር ላይ ሲሆኑ አልፎ አልፎም የተኩስ ድምፅ ይሰማል፡፡

ፖሊስ ሴቶችንም ወንዶችንም ሽማግሌ ህፃን ሳይል በማሰር ላይ የሚገኝ ሲሆን የአካባቢው ወንዶች የት እንደደረሱ የታወቀ ነገር የለም። ሚስቶቻቸው እህት እናቶቻቸው አባት ወንድሞቻቸው በአጠቃላይ እዛ አካባቢ ያለው ሁሉ ወደ እስር ቤት ተግዘዋል፡፡ ይህ ተኩስ ልውውጥ ላይ እንደ አይን እማኞች ከሆነ ከበርካታ የባህርዳር ቀበሌዎች የተሰባሰበ ህብረተሰብ ከሰፈሩ ሰዎች ጋር በመተባበር ፖሊስና ልዩ ሃይልን በጋራ ሲያባርር እንደነበር ገልፀዋል፡፡

በዛሬው የባህርዳሩ ግጭት ለጊዜው የአባቱ ስም ያልታወቀ ጨመረ የተባለ ወጣት ግንባሩ ላይ በጥይት ተመትቶ አስከሬኑ ወደ ሆስፒታል ሲወሰድ ፖሊሶች ቀምተው አስከሬኑን አንሰጥም ማለታቸውም ተሰምቷል።

ለዘ-ሐበሻ መረጃውን ያደረሱ ወገኖች እንዳሉት ይህ ግጭት ለጊዜው አሁን ትንሽ ጋብ ያለ ቢሆንም አልፎ አልፎ በዚህ ሰዓትም ተኩስ ድምፅ ይሰማል፡፡ እነዚህ አካባቢዎች እና ቀበሌዎችለፖሊስ ኢፍትሃዊ ድርጊት አንገዛም፤ ላቤን ጠብ አድርጌ አፈር ቆፍሬ ደክሜ የሰራሁትን ቤት ሲያሰኝህ እየመጣህ ልታፈርሰው አትችልምም፣ ፈቃድ አውጥቼ ስንት ጊዜ በሙሰኛ ባለስልጣናት ተበዝብዤ የሰራሁትን ቤቴን ሌላ መውደቂያ ሳይኖረኝማ አታፈርሰውምብለው ለበርካታ አመታት ሲደክሙ ቆዩትን ቤት በሌሊት እንደ ሽፍታ የማፍረሻ ትዕዛዝ ሳያሳዩ ለማፍረስ መሞከር ህገወጥነት ሆኖ እያለ የንፁሃንን ደም በከንቱ ማፍሰስ የመንግስትን ወሮ በላነትና የፖሊስን ደደብነት የሚያሳይ አሮጋንተነት ነው ሲሉ አስተያየታቸውን የባህርዳር ነዋሪዎች ይሰጣሉ፡፡
ተጨማሪ ዘገባዎችን እንደደረሱን እንመለሳለን።

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/29034

No comments:

Post a Comment