Friday, April 10, 2015

በወልቃይት ወረዳ የፌደራል ፖሊሶች ባደረሱት ድብደባ የአንድ ሰው ሕይወት ጠፋ ከሁመራ እስከ ትክል ድንጋይ ወታደሮች ሴት እህቶቻችን ላይ ወሲባዊ ጥቃት ይፈጽማሉ

በትግራይ ምእራባዊ ዞን ወልቃይት ወረዳ ማይ ገባ ከተማ ውስጥ የሚገኙ የፌደራል ፖሊስ በአካባቢው የሚገኙትን እለታዊ ስራቸውን በሚያከናውኑ ንፁኃን ሰዎች ላይ የተቃዋሚ ድርጅት ተላላኪዎች ናችሁ በማለት በደል እያደርሱባቸው እንደሚገኙ ተገለፀ ሲል ደህሚት አስታወቀ::

በምንጮቹን ጠቅሶ ደህሚት እንደዘገበው በወልቃይት ወረዳ ማይ ገባ ከተማ ውስጥ የሚገኙ የስርአቱ ፌደራል ፖሊስ አባላት ሰርተው ኑሮአቸውን የሚመሩ ዜጎቻችንን የትጥቅ ትግል ለሚያካሂዱ ድርጅቶች የተላካችሁ ናችሁ፤ በረሃ ላይ የደበቃችሁትን መሳሪያም አስረክቡን በማለት መጋቢት 1/2007 ዓ/ም በርካታ ንፁሃን ወገኖች በገመድ አስረው እየደበደቧቸው መዋላቸውን ለማወቅ ተችሏል::

መረጃው ጨምሮ እንዳስረዳው ምንም አይነት ወንጀል ሳይኖራቸው ባስከፊ ሁኔታ እየተደበደቡ የዋሉት በርካታ ወገኖች ቢሆኑም በተለይ ወርቅ ለቀማ ላይ የነበሩትን 6 ሰዎች በአስከፊ ሁኔታ ተደብድበው ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን ከተደበደቡት ውስጥም የአስገደ ፅንብላ ተወላጅ የሆነው ሓዱሽ ታፈር የተባለ ንፁህ ወገን ወድያውኑ መሞቱን መረጃው አክሎ አስረድቷል::

በሌላ ዜና ከሁመራ እስከ ትክል ድንጋይ ድረስ ያሉት የስርዓቱ ወታደሮች ህዝቡን እያንገላቱት መሆናቸውን ምንጮች አስታወቁ ሲል ደህሚት ዘግቧል::


በመረጃው መሰረት ከተለያዩ ክፍሎች የተውጣጡ አዲስ ወታደሮች ከሁመራ ጀምረው እስከ ትክል ድንጋይና ሌሎች አካባቢዎች ሰፍረው እንደሚገኙና በተለይ በትግራይ ምእራባዊ ዞን ህዝቡ ከቦታ ወደ ቦታ ተንቀሳቅሶ እለታዊ ኑሮውን እንዳይመራ እንቅፋት ሁኖው እንደሚገኙ ተገለፀ::

መረጃው በማስከተል እነዚህ ከስነ ምግባር ውጭ የሆኑ ወታደሮች በሴት እህቶቻችን ላይ ወሲባዊ አመፅ እየፈፀሙ ስለሚገኙ። በኤች አይ ቪ ኤዲስና ሌሎች ተላላፊ በሽታዎች እየተጠቁ በመሆናቸው ምክንያት ወላጅ የሌላቸውን ልጆች ለማሳደግም በመገደዳቸው ምክኒያት ነዋሪው ህዝብም ድርግቱ መፍትሄ እንዲደረግለት በማለት ወደ ሚመለከታቸው አካላት ያቀረበውን ጥያቄ እስካሁን መፍትሄ እንዳላገኘበት ለማወቅ ተችሏል::


http://www.zehabesha.com/amharic/archives/40419

No comments:

Post a Comment