Monday, April 6, 2015

(መልካም ዜና) የፋሺሽቱ የግራዚያኒ ኃውልት ስያሜ እንዲወገድ ውሳኔ ተላለፈ

እንደሚታወቀው፤ “የኢትዮጵያ ጨፍጫፊ” በመባል ለሚታወቀው ለሮዶልፎ ግራዚያኒ፤ አፊሌ በምትሰኝ የኢጣልያ ከተማ አንድ የመታሰቢያ ኃውልትና መናፈሻ ተቋቁሞለት፤ የቫቲካን ተወካይ በተገኙበት፤ እ.አ.አ. በነሐሴ 2012 ተመርቆለት ነበር። በኢትዮጵያ ላይ እጅግ አስከፊ የጦር ወንጀል በማስፈጸም ለታወቀው ፋሺሽት ይህንን የመስለ ተግባር ተቀባይነት ስለ ሌለው ማሕበራችን፤ በዓለም አቀፍ ደረጃ፤ በሚገኙ ኢትዮጵያውያንና የኢትዮጵያ ወዳጆች እንዲሁም በመንፈሳዊና በሌሎችም ድርጅቶች ድጋፍ ጭምር ተቃውሞውን በልዩ ልዩ መንገድ ሲገልጽ ከርሟል።

ጥረቱም ሁሉ፤ በቸሩ የኢትዮጵያ አምላክ እርዳታ፤ መልካም ውጤት ማስገኘት ጀምሯል። ባለፈው ወር፤ እ.አ.አ. መጋቢት 13 ቀን 2015 አፊሌ ከተማ የምትገኝበት የላዚዮ አውራጃ ምክር ቤት ባሳለፈው ውሳኔ የግራዚያኒ ስያሜ በ15 ቀን ውስጥ እንዲወገድ፤ አለበለዚያ ለመታሰቢያ ኃውልቱ የወጣው ገንዘብ እንዲመለስና ተጨማሪ እርምጃም እንደሚወሰድ ገልጿል። የውሳኔውን ዋና ዋና ነጥቦች ከዚህ በታች መመልከት ይቻላል።

በዚህ አጋጣሜ፤ ስለ ኃውልቱ ለተገኘው መልካም ውጤት በድጋፋቸው ለተባበሩት ሁሉ ማሕበሩ ጥልቅ ምሥጋናውን በትሕትና ይገልጻል።

የላዚዮ አውራጃ ኦፊሴያላዊ መግለጫ፤ (ቁ. 24/1) ዋና ዋና ነጥቦች
(ዶር. ግርማ አበበ በኢጣልያንኛው ሰነድ መሠረት በእንግሊዝኛ ባቀረቡት መሠረት)
ጉዳዩ፤ የአፊሌ ከተማ ማሕበራዊ ምክር ቤት ለማርሻል ሮዶልፎ ግራዚያኒ አፌሌ
ስለ መረቀው ትንሽ የሚሊታሪ ሚዩዚየም፤ እ.አ.አ. ሐምሌ 21 ቀን 2012
ያስተላለፈውን ውሳኔ እንዲሰርዝ የቀረበ ጥሪ፤


በላዚዮ አውራጃ የተወሰደ እርምጃ
እ.አ.አ. መጋቢት 13 ቀን 2015
እ.አ.አ. ሕዳር 11 ቀን 2004 የወጣውን የላዚዮን አውራጃ ሕግና ሌሎችንም ጉዳዮች በመመልከት፤
በተጨማሪም እ.አ.አ. በየካቲት 18 ቀን 2002 የወጣውን የክልሉን ሕግ በማስታወስ፤


የአፊሌ (ከተማ) ማሕበረሰብ ምክር ቤት እ.አ.አ. በሐምሌ 21 ቀን 2012 አንድ ትንሽ የሚሊታሪ ሚዩዚየም ለማርሻል ሮዶልፎ ግራዚያኒ እንዲመረቅ የወሰነ መሆኑን በማሰብ፤ ሮዶልፎ ግራዚያኒ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የወንጀለኞች ዝርዝር የተመዘገበ፤ በሰዎች ላይ የመርዝ ጋዝ የተጠቀመና በኢትዮጵያ የቀይ መስቀል ሆስፒታል በቦምብ እንዲደበደብ ትእዛዝ ያስተላለፈ በፋሺሽት ኢጣልያ ቁልፍ መሪ የነበረ መሆኑን በማስታወስ፤

የአፊሌ ማሕበረሰብ ምክር ቤት ትንሹን የሚሊታሪ ሚዩዚየም ለማርሻል ሮዶልፎ ግራዚያኒ በመመረቅ ያስተላለፈውን ውሳኔ እንዲሰርዝ፤ ይህንንም ተግባር፤ የላዚዮ ባለሥልጣን እ.አ.አ. በመጋቢት 13 ቀን 2015 ከወሰነበት ቀን ጀምሮ በ15 ቀኖች ውስጥ እንዲፈጽም ታዟል።

የማሕበረሰቡ ምክር ቤት ውሳኔውን እንዲሰርዝ የተላለፈለትን ትእዛዝ በተፈቀደለት ጊዜ ውስጥ ካላጠናቀቀ፤ ለትንሹ የሚሊታሪ ሚዩዚየም መሥሪያ በአውራጃው ባለሥልጣን የተሰጠውን ገንዘብ እንዲመልስ ይጠይቃል።


በመጨረሻውም፤ የአፊሌ ማሕበረሰብ ምክር ቤት በአውራጃው ባለሥልጣን የተጠየቀውን ሳይፈጽም ቢቀር፤ ባለሥልጣኑ ጉዳዩን፤ የአፊሌ ከተማ ምክር ቤትን ውሳኔ፤ ወደ ፍርድ ለማቅረብ አስፈላጊውን እርምጃ ይወስዳል።


ማሳሰቢያ፤ ፋሺሽት ኢጣልያ በውድ ሐገራችን በኢትዮጵያ ላይ በፈጸመችው የጦር ወንጀል ስለ ተጨፈጨፉት አንድ ሚሊዮን ወገኖቻችን፤ ስለ ወደመውና ስለ ተዘረፈው ንብረት ተገቢው ፍትሕ፤ ብቁ የሆነ ካሣና ይቅርታ የመጠየቅ ተግባር እንዲከሰት በመከናወን ላይ ስላለው ጥረት ዝርዝሩን በwww.globalallianceforethiopia.org መመልከት ይቻላል።

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/40329

No comments:

Post a Comment