Wednesday, April 22, 2015

መንግስት በአ.አ የጠራው ሰልፍ ወደ ተቃውሞ ተለወጠ * ሴቶች እና አዛውንቶችን ሳይቀር ደብደበ * አስለቃሽ ጭስ ተተኮሰ * የሕዝቡ ቁጣ አልበረደም

የአይ ኤስ አይ ኤስን ጭካኔ ለመቃወም ሰልፍ የወጡ ኢትዮጵያውያን አገራቸው ውስጥ ሌላ ጭካኔ ገጥሟቸዋል

(ዘ-ሐበሻ) በአዲስ አበባ ኢሕአዴግ ለፖለቲካ ጥቅም ማግኛ ሲል የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ወደ ተቃውሞ ተለወጠ:: ማንኛውም ሕዝብ ሰላማዊ ሰልፍ እንዳያደርግ የሚከለከለው ኢሕአዴግ ሕዝብን ወዳጅ መስሎ ቢቀርብም በመስቀል አደባባይ ዳግም ሕዝብን በመደብደብ ዳግም ራሱን ማዋረዱን ከአዲስ አበባ የደረሰን መረጃ አመልክቷል::

በዛሬው ኢሕአዴግ በጠራው ሰልፍ ላይ ሕዝቡ ተቀላቅሎ በመግባት ተቃውሞውን በመንግስት ላይ ያሰማ ሲሆን “እኛን ከምትደበድቡ አይሲስን ደብድቡ” “ወታደር ዳርፉር ከምትልኩ ሊቢያ ላኩ” እያለ ተቃውሞውን አሰምቷል:: “ወኔ የሌለው የሃገር ሸክም ነው” እያለ ተቃውሞውን ያሰማው የአዲስ አበባ ሕዝብ ከደህንነቶች ጋር ግብግብ የገጠመ ሲሆን በዚህም በርካታ ወጣቶች በፌደራል ፖሊሶች ተይዘው መታሰራቸው ታውቋል::


የአዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከልን እንደ እስር ቤት በመጠቀም ስርዓቱ በርካታ ወጣቶችን ያሰረ ሲሆን በቆመጥ ሴቶችን እና አዛውንቶችን ሳይለይ ቀጥቅጧል:: አስለቃሽ ጭስ በመጠቀምም ተቃውሞውን ለማብረድ ጥሯል::

በጨርቆስ፣ መስቀል አደባባይ፣ ተክለሃይማኖት እና ሌሎችም አካባቢዎች ተቃውሞው እንደቀጠለ ይገኛል::

በሰልፉ ላይ ንግግር ለማድረግ የመጡት አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ሊናገሩ ሲሉ ሕዝቡ በጩኸት ተቃውሞውን
‹‹ውሸት ሰለችን ሰለችን!››
‹‹ዋ! ዋ! ዋ!››
‹‹ታርዷል ወገኔ!››
‹‹መንግስት የሌለው እዚህ ብቻ ነው!›› ሲል ተቃውሞን ከመግለጹ በተጨማሪ ጆሮውን በመያዝና ፊቱን በማዞር ቁጣውን ገልጿል ሲል ለዘ-ሐበሻ የደረሰው መረጃ አመልክቷል::


ከአዲስ አበባ የደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው የመንግስት ፌደራል ፖሊሶች አሁንም በአራቱም አቅጣጫ ህዝቡን እየተከታተለ እየደበደበና እያሰረ ነው፡፡ በርካታ አዛውንቶችና ወጣቶች ራሳቸውን ስተው ወድቀዋል፡፡

ከተበተነው ህዝብ መካከልም ፖሊስ የተቃውሞው መሪ ናቸው በሚል ወጣቶችን እየነጠለ ማሰር ጀምሯል፡፡ በሰልፉ ላይ ተሳታፊ የነበሩት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ዕጩዎች እየታሰሩ መሆኑ የተሰማ ሲሆን የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩ የሆነው ይድነቃቸው አዲስን ጨምሮ ሌሎች አመራሮችና አባላት ታስረዋል፡፡


በኢትዮጵያውያን ላይ የጭካኔ እርምጃ የወሰደው አይ ኤስ አይ ኤስ ላይ እርምጃ አልወሰድክም፣ ለዜጎች ትኩረት አልሰጠህም በሚል ተቃውሞ የገጠመው መንግስት በኢትዮጵያውያን ላይ ሌላ ጭካኔ እየፈፀመ መሆኑ የራሱን የስር ዓቱን ደጋፊዎች ሳይቀር አሳዝኗል::


http://www.zehabesha.com/amharic/archives/40745

No comments:

Post a Comment