Thursday, April 30, 2015

ግብፅ፤ በምስራቅ ሊቢያ የሚገኘውን የአይ.ኤስ.አይ.ኤስ መቀመጫ ለመደምሰስ ዝግጅቷን አጠናቀቀች

የግብፅ መንግስት በምስራቃዊ ሊቢያ ዴርና ከተማ የከተመውን አይ.ኤስ.አይ.ኤስ አሸባሪ ኃይል ለመደምሰስ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን የወታደራዊና የደህንነት መረጃዎችን በማጠናከር የሚዘግበው ዴብካ ፋይል ድረ ገጽ ይፋ አደረገ።

ግብፅ ከፍተኛ መጠን ያለው የምድር ጦር እና አየር ሃይሏን በማቀናጀት በምስራቅ ሊቢያ የሚገኘውን የአይ.ኤስ.አይ.ኤስ አሸባሪ ኃይል ለመደምሰስ እና ምስራቅ ሊቢያን ለመቆጣጠር የግብፅ ወታደራዊ ሃይል በተጠንቅ መሆኑ ታውቋል።

ግብፅ ይህን ወታደራዊ ዘመቻ የምታከናውነው ፕሬዚዳት አብዱል ፈታህ አል-ሲሲ በደረሳቸው የሀገር ውስጥ ደህንነት መረጃ ሲሆን የደህንነት መረጃዎቹ እንደሚያሳዩት በምስራቅ ሊቢያ የከተመው የአይ.ኤስ.አይ.ኤስ አሸባሪ ቡድን በግብጽ ብሔራዊ ደህንንት ላይ አደጋ መጋረጡን ነው። ይህም ሲባል፣ የእስልምና መንግስትን ለመመሥረት ያቀዱት እነዚሁ አሸባሪዎች በአንዳንድ የግብፅ ከተሞች ሰርገው መግባታቸው ተረጋግጧል። እንዲሁም በግብጽ ጦር ሰራዊት ውስጥም መስረጋቸው የደህንነት መረጃዎች አሳይተዋል።

የአይ.ኤስ.አይ.ኤስ አሸባሪ ቡድን በበኩሉ የግብፅ እንቅስቃሴ ስላሰጋው ከኢራቅ እና ከሶሪያ አሸባሪ ሃይሎችን እያመጣ ወታደራዊ እቅሙን እያጠናከረ እንደሚገኝ ለማወቅ መቻሉን ዘገባው ያሳያል። ከሶሪያ የሚንቀሳቀሰው ሃይል በአየርና በሜዲትሪያን ባሕር ወደሊቢያ የሚገባ ሲሆን፣ ከኢራቅ የሚንቀሳቀሰው አሸባሪ ሃይል በሲናይ ፔኒንሱላ በኩል እንዲሁም በነዳጅና በሃሺሽ አዟሪዎች እገዛ በሲውዝ ካናል ግብፅ አድርገው ምስራቅ ሊቢያ እየገቡ ነው።

ዴብካ ፋይል እንደሚለው ግብፅ በሊቢያ ላይ ወረራ ለመፈጸም መዘጋጀቷ በአሜሪካ መንግስት የአጀንዳ ቅደም ተከተል ቁጥር አንድ ቦታ መያዙን አስነብቧል። ይህም በመሆኑ የአሜሪካው የሲ.አይ.ኤ. ዳሬክተር ጆን በርናንስ ያለረተጠበቀ ጉብኝት በካይሮ አድርገዋል። ከግብፅ ፕሬዝደንትም ጋር ውይይት መቀመጣቸው ታውቋል። ግብፅ በሊቢያ ላይ ልትከፍተው ላሰበችው ወረራ ማምራሪያ የጠየቁት የሲ.አይ.ኤ.ው ዳይሬክተር ከግብፅ መንግስት ዋስትና ያለው መግለጫ ቀርቦላቸዋል። ይሄውም፣ ፕሬዝደንት ኤል ሲሲ በሰጡት የዋስትና ማረጋገጫ ላይ እንዳሉት የግብፅ ጦር ሰራዊት ሊቢያ ውስጥ ገብቶ የመቆየት ፍላጎት የለውም። ጂሃዲስቱን ካሸነፉና ጦር መሳሪያውንም ካስፈቱት በኋላ በምስራቅ ሊቢያ በሚገኘው ቱብሩክ ከተማ ላለው የሊቢያ ጦር አሳልፈው እንደሚሰጡት አስታውቀዋል። የቱብሩክ ከተማ አስተዳደር የተመሰረተው በሊቢያ የፓርላማ አባሎች ሲሆን፣ ቲሪፖሊ በፅንፈኛ ሃይሎች እጅ በመውደቋ ምክንያት ነበር ወደዚህ ከተማ ሸሽተው የመጡት፡

አሜሪካ ሙሉ ለሙሉ ግብፅ ሊቢያን ለመውረር ያደረገችውን ዝግጀት ባትደግፈውም፣ ፕሬዝደንት ኤል ሲሲ ግን በሀገራቸው ላይ የተደቀነውን የአሸባሪዎች አደጋን ለመዋጋት ቁርጠኛ አቋም መውሰዳቸው ተዘግቧል።

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/41050

No comments:

Post a Comment