Thursday, February 7, 2013

የሚገነፍል ድስት የሚያበላሸዉ እራሱን ነዉ

ግንቦት 7 መግለጫ


በአለፉት ሁለትና ሦስት አመታት ዘረኞቹ የደደቢት ተዋንያን በተከታታይ ለህዘብ ካሳዩት ድራማና የኢትዮጵያ ህዝብም አይቶ እንዳላየ ታዝቦ ካለፋቸዉ የወያኔ ጉዶች ዉስጥ አንዱና ዋነኛዉ የህዝብ ትግል አቅጣጫ በቀየረና እምርታ በአሳየ ቁጥር የወያኔ ጀሌዎች ባልተባ ብዕራቸዉ እየጻፉና ባልተካነ ችሎታቸዉ እየከየኑ እንደቤት ዉስጥ እቃቸዉ በሚቆጣጠሩት የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ለህዝብ የሚያቀርቡት ሰዉ ሰዉ የማይሸት የባዶ ድራማ ትርኢት ነዉ። ይህ ለዜጎች መብትና ነጻነት መከበር በህይወታቸዉ ቆርጠዉ የሚታገሉ የህዝብ ልጆችን በሽብርተኝነት እየፈረጀ በድራማ መልክ ተቀነባብሮ ለትግሉ ባለቤት ለሆነዉ የኢትዮጵያ ህዘብ የሚቀርበዉ ጥራዝ ነጠቅ ትርኢት ወያኔ ለኢትዮጵያ ህዝብ ያለዉን ንቀት በግልጽ ከማሳየት ዉጭ ሌላ የሚፈይደዉ ነገር አለ ብለዉ የሚያምኑ ካሉ እንደ ወያኔ የህዝብን ታላቅነት የሳቱና ህዝብን የሚንቁ ኃይሎች ብቻ ናቸዉ። በእርግጥም ይህ ተደራሲዉን በዉል ለይቶ የማያዉቅ ድራማ በግልጽ የሚነግረን አንድ ነገር ቢኖር ሽብርተኛ ተብለዉ ፍርድ ቤት መቅረብ ያለባቸዉ ሰላማዊ ዜጎችን እያደኑ የሚያስሩት፤ የሚደበድቡትና የሚገድሉት ዘረኞቹ የወያኔ ባለስልጣኖች ብቻ መሆናቸዉን ነዉ።
የዛሬ ሁለት አመት ግንቦት ሰባትን፤ የኦሮሞ ነጻነት ግንባርንና አገር ቤት ሽንጣቸዉን ገትረዉ የሚታገሉትን እነ እስክንድር ነጋን፤ ርእዮት አለሙን፤ ኦብላና ሌሊሳን፤ በቀለ ገርባንና አንዱአለም አራጌን ሽብርተኞች ናቸዉ ብሎ የኢትዮጵያን ህዝብ ለማሳመን “አኬልዳማ” የሚል የቂል ድራማ ሰርቶ ያሳቀን ወያኔ ዘንድሮ ደግሞ መብቴ ይከበር ብሎ ከአንድ አመት በላይ በሰላማዊ መንገድ የታገለዉን የኢትዮጵያን ሙስሊም ህብረተሰብ ከለየላቸዉ አሸባሪዎች ከአልቃይዳና ከአልሽባብ ጋር የሚያዛምድ “ጅሃዳዊ ሐረካት” የሚባል ድራማ አዘጋጀቶ ከሰሞኑ ለህዝብ አሳይቷል። ግንቦት ሰባት የፍትህ፤የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ይህንን ሁለቱን ትልልቅና ጥንታዊ የኢትዮጵያ ሐይማኖቶች ለማጣላት ሆን ተብሎ የተሰራዉን የወያኔ ድራማ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ እንዳቀራረቡ ሳይሆን በጥንቃቄ አንዲመለከተዉና የወየኔን ህዝብን የማጋጨትና አገር የማፍረስ ሴራ እንዲያከሽፍ በአደራ ጭምር ያስጠነቅቃል።
ኢትዮጵያ እስልምናንም ሆነ ክርስትናን በቅድምያ ከተቀበሉ አገሮች አንዷ መሆኗ ብቻ ሳይሆን ክርስትናና እስልምና ከአንድ ሺ አመታት በላይ በሠላም ተከባብረዉ ጎን ለጎን የኖሩባት ብቸኛ አገር ናት። የአገር አንድነትና የህዝብ ሠላም እረፍት የሚነሳዉ ወያኔ ግን ይህንን ዘመናት ያስቆጠረ ታሪክ ለመለወጥና የህዝብን በሠላም አብሮ መኖር ለማደፍረስ ቆርጦ የተነሳ ይመስላል። የኢትዮጵያ ህዝብ በሠላም ኖረም አልኖረ ወያኔ “ሠላም” የሚለዉ የኢትዮጵያ ህዝብ እየተረገጠ አንገቱን ደፍቶ እስከተገዛለት ድረስ ብቻ ነዉ። ወያኔ ሰሞኑን “ጅሃዳዊ ሐረካት” የሚል ድራማ ሰርቶ ለህዝብ ማስተላለፍ የፈለገዉ መልዕክትም በሠላም መኖር ከፈለጋችሁ እኔ የምላችሁን ብቻ ስሙ ካለዚያ ጂሃዲስቶች እጅ ትወድቃላችሁ የሚል ነዉ። ግንቦት ሰባት ይህንን ቅንጣት ታክል ተአማኒነት የሌለዉ የወያኔ መልዕልት የሚሰማ ህሊና ያለዉ ኢትዮጵያዊ አለ ብሎ ባያምንም የተደጋጋመ ዉሸት አንዳንዴ እዉነት የመምሰል ዝንባሌ ስላለዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ከዚህ አይነቱ አደጋ እራሱን እንዲጠብቅ ከወዲሁ ያስጠነቅቃል። ወያኔ በተጨነቀ ቁጥር የቂሎች ድራማን መስራት ባህሪው ነው።
ግንቦት ሰባት የፍትህ፤የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ የዛሬ ሁለት አመት አኬልደማን አይቶ ትግሉን አጠናክሮ የቀጠለዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬም ጅሃዳዊ ሐረካትን አይቶ የጀመረዉን ትግል ከፍጻሜዉ ለማድረስ በተጠንቀቅ እንዲቆም ወገናዊ ጥሪዉን ያለስተላልፋል። የዘረኞች ስርዓት ሙሉ ለሙሉ እስካልተደመሰሰ ድረስ ኢትዮጵያ ዉስጥ በተናጠል መብቱና ነጻነቱ የሚከበር የህብረተሰብ ክፍል የለምና የእስልምና እምነት ተከታዮች ጀመሩትን የመብትና የነጻነት ትግል የኢትዮጵያ ህዝብ እንደራሱ ትግል አድርጎ በማቀፍ እራሱን ከዘረኞችና ከዘራፊዎች ነጻ እንዲያወጣ ግንቦት ሰባት የትግል ጥሪዉን ያስተላልፋል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

Postd By.Dawit Demelash

No comments:

Post a Comment