Saturday, November 9, 2013

የቱርኩ አይካ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ በኢትዮጵያውያኑ ላይ በሃገራቸው በደል እየፈጸመ ነው ሲሉ ሰራተኞች አማረሩ

በሰበታ ዓለም ገና አካባቢ የሚገኘው የቱርኩ የጨርቃጨርቅ ፋብሪካ አይካ በኢትዮጵያውያን ሴት ሰራተኞች ላይ በገዛ ሃገራቸው በአረብ ሃገራት ከሚደርስባቸው በደል ያልተናነሰ ጭቆና እያደረሰባቸው እንደሚገኝ የድርጅቱ ሠራተኞች በደላቸውን ለዘ-ሐበሻ ገለጹ። የሰው ልጅ በፈጣሪ ዘንድ እኩል እንደሚታይ የሚገልጹት እነዚሁ ሰራተኞች ድርጅቱ ሠራተኛ ሲቀጥር መልክ እና ቁመና እንደሚያይና በዚህም በደል እንደሚፈጽም ገልጸዋል፡፡

እነዚህ ሠራተኞች በቀን 10 ሰዓት እንዲሰሩ እንደሚደረጉ ያስታወቁት እነዚሁ ጠቋሚዎች በወር 400 እስከ 600 ብር ብቻ እንደሚከፈላቸው ተናግረዋል። በተለይም ማንኛውም ሠራተኛ ወደ ሥራ ቦታ ሲገባ ስልኩን እና ቦርሳውን እንዲያስቀምጥ እንደሚገደድ ያስታወቁት እነዚሁ ሠራተኞች በሥራ ሰዓት ከማንም ጋር እንዳይገናኙ እንደሚደረጉ አጋልጠዋል።
በአይካ ኩባንያ ውስጥ የሚሰሩ ቱርካውያን የወሲብ ጥቃት እንደሚፈጽሙባቸው ያስታወቁት እነዚሁ ዕማኞች ሠራተኞች ከሥራ እንባረራለን በሚል ፍራቻ ምስጢራቸውን አፍነው እንደሚቀመጡ፤ አፍ አውጥተው ለመናገር የደፈሩም በቶሎ ከስራ እንደሚባረሩ ጠቁመዋል። -ሐበሻ በዚህ ዙሪያ ከአይካ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ አመራሮች የሚሰጡትን አስተያየት ለማከል ያደርገችው ጥረት አልተሳካም።
ኢትዮጵያውያን በሃገራቸው የሚደርስባቸውን ጭቆና እና በደል በመሸሽ በአረብ ሃገራት በመሄድ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት እንደሚፈጸምባቸው ይታወቃል። ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግስታዊ ሚድያዎች ይህን በደል እንዳልሰሙ በመሆን በአይካ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ዙሪያ ሰሞኑን ያሰራጩት ዜና የሚከተለው ነው፦
አይካ አዲስ የተባለው የቱርክ ኩባንያ በኢትዮጵያ ውስጥ በስፋት እያካሔደ ላለው ፕሮጀክት መንግሥት ያላሰለሰ ድጋፍ እንደሚያደርግ ፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ አስታወቁ፡፡
ዶክተር ሙላቱ ትናንት የአይካ አዲስ ጨርቃጨርቅና ኢንቨስትመንት ኩባንያ ባለቤትና የቦርድ ሊቀመንበርን ሚስተር ዩሱፍ አይደንዝን በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ዶክተር ሙላቱ በዚሁ ወቅት እንዳስታወቁት፣ አይካ አዲስ በሀገሪቱ የሚያካሂደው ማንኛውም የልማት ፕሮጀክት መንግሥት ያላሰለሰ ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል፡፡

የአይካ አዲስ ቴክስታይልና ኢንቨስትመንት ኩባንያ ባለቤትና የቦርድ ሊቀመንበር ሚስተር ዩሱፍ አይደንዝን በበኩላቸው፤ ኩባንያቸው በኢትዮጵያ ውስጥ በሚያካሒደው የጨርቃጨርቅ ልማት እስከ 50 ለሚሆኑ ሰዎች የሚደርስ የሥራ እድል ፈጥሯል፡፡ በአሁኑ ወቅት ኩባንያው የሚያመርተውን ጨርቃጨርቅ ወደ አውሮፓና ሌሎች አገሮች በመላክና የውጭ ምንዛሪ በማስገኝት የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ጠቁመዋል፡፡
በአይካ አዲስ ቴክስታይልና ኢንቨስትመንት ኩባንያ አማካኝነትም በርካታ የቱርክ ኩባንያዎችና ባለሀብቶች ወደ ኢትዮጵያ እየመጡ መሆኑንም ሊቀመንበሩ አመልክተዋል፡፡
   
       Posteed By.Dawit Demelash

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/9132

No comments:

Post a Comment