Wednesday, November 20, 2013

ለዜጎች ስደት እንዲሁም በስደት ለሚደርስባቸው ሰቆቃ ተጠያቂ ሥርዓቱን የሚመራው ወያኔ/ህውሃት ነው!!

November 19, 2013
ዳዊት ደመላሽ
dawitdemelash@gmail.com
ቀደም ባሉት ዘመናት ወደ ውጭ ሀገር በተለያየ ምክንያት የተጓዙ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ወደ ሀገራቸው የሚመለሱበትን፤ የእናት ሀገራቸውን ምድር የሚረግጡበትን ቀናት ይቆጥሩና ይናፍቁ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን በዋናነት ወደ ውጪ ሀገር የሚሄዱት ለትምህርት ሲሆን የዚያን ዘመን ወጣት ትምህርቱን ጨርሶ በመመለስ የሀገሩን እና የሕዝቡን ውለታ ለመክፈል የነበረው ጉጉት ከፍተኛ ነበር፡፡ ተምሮ በውጪ ሀገር መቅረት ሀገርን እንደመክዳት የሚያስቆጥር በመሆኑ በኢትዮጵያውያን ህሊና ስደት ተቀባይነት አልነበረውም፡፡
ዛሬ ዛሬ ሁኔታዎች ሁሉ ተለዋውጠው የኢትዮጵያ ህዝብ እጣ ፋንታ ፍልሰትና ስደት ሆኗል፡፡ ስደት የማያባራ የኢትዮጵያውን የሕይወት ገጽታ ሆኗል፡፡ የገጠሩም የከተማውም ሰው ወደ ውጭ ሀገር ይሰደዳል፡፡ ወጣቶች ይሰደዳሉ፡፡ እህቶቻችን ይሰደዳሉ፡፡ ሕፃናት ጭምር በጉዲፈቻ ስም ይሰደዳሉ፡፡ ‹ሕጋዊ› በተባለውም ሆነ በሕገ-ወጥ መንገድ ሕዝባችን ወደ ውጭ ሀገር ይነጉዳል፡፡ በዚህ የተነሳም በወሊድ ምጣኔ ሳይሆን በሰደት ምክንያት አምራች የሆነው የህዝብ ቁጥር ሊቀንስባቸው ከሚችሉ ሀገሮች ኢትዮጵያ አንዷ ሆናለች፡፡
ለዚህ ሁሉ ማለቂያ የሌለው ስደት መንስኤው በደርግ ተጀምሮ በወያኔ/ህውሃት ተጠናክሮ የቀጠለው አምባገነናዊ አገዛዝ የፈጠረው አስከፊ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ፖሊሲ ውድቀት መሆኑ አይካድም፡፡ ዜጎች በሀገራችን ከተንሠራፋው ድህነትና ሥራ አጥነት በማምለጥ ሠርቶ ለማግኘትና የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ህይወት ለመለወጥ ስደትን ቢሹም ከኢኮኖሚያዊ ፍላጎት በስተጀርባ አምባገነናዊ የፖለቲካ ሥርዓቱ የወለዳቸው ችግሮቹ ለስደቱ መንስኤነት ዋነኛውን ሚና ይጫወታሉ፡፡
የሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነት አለመረጋገጥ፣ ለሕዝብ ፍላጎት ተገዢና ተጠያቂ መንግሥት አለመኖር፣ የሕግ የበላይነት አለመከበር፣ የፍትሕ፣ የመልካም አስተዳደርና የዴሞክራሲ እጦት፣ በዜጎች ላይ በቀበሌ ካድሬዎች የሚደርስ አፈናና ወከባ፣ ከመሬትና ከንብረት መፈናቀል እንዲሁም የወያኔ/ህውሃት የተሳሳተ የትምህርት ፖሊሲ ውጤት ለዜጎቻችን ስደትና ወጥቶ ላለመመለስ ዋነኛ ምክንያቶች ናቸው፡፡
ባለንበት የግሎባላይዜሽን ዘመን የሰው ልጅ በተለያየ ምክንያት ከሀገር ወደ ሀገር በስፋት ይንቀሳቀሳል፡፡ ከሀገሩም ወጥቶ በተለያዩ ሀገሮች ኑሮውን መስርቶ ይኖራል፡፡ የየሀገሩ መንግሥታት በሌላ ሀገር የሚኖሩ ዜጎቻቸውን መብት ለማስከበር የሚከተሉት ፖሊሲና የሚወስዱት ዲፕሎማሲያዊ ርምጃ ዜጎቻቸውን የሚያኮራና የሚያስከብር ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በተቃራኒው የኛ ሀገር መንግሥት  ተብዬው ግን በውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን የሚፈልጋቸው ለኢንቨስትመንት ለሚያውሉት ገንዘባቸው ካልሆነ በስተቀር በሰው ሀገር ለሚደርስባቸው ውርደትና አስከፊ ሰቆቃ መድህን ሲሆናቸው አይታይም፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት በሊባኖስ በአሠሪዋ ስቃይ የደረሰባትና ራሷን ያጠፋችው የዓለም ደቻሳ ሁኔታ የኢትዮጵያውያንን አንገት ያስደፋ ሲሆን መንግሥት ተብዬው ለዜጎቹ ህልውናና ክብር ደንታ ቢስ መሆኑን በገሀድ አስመስክሯል፡፡
በሌላም በኩል ዜጎቹ በሕገ-ወጥ ደላሎች አማካይነት በሁሉም የጎረቤት አገሮች በኩል ወደ ተለያዩ ሀገራት በመሰደድ መጉላላትና አደጋ ሲደርስባቸው የወያኔ/ህውሃት የሕገ-ወጥ ደላሎች ቁጥር መጨመሩን በልማታዊ ጋዜጠኞቹ በሚዲያው ከሚነግረን በቀር ጉዳዬ ብሎ ችግሩን ከምንጩ ለመቅረፍ የሚወስደው እርምጃ ባለመኖሩ መንግሥታዊ ኃላፊነቱን መወጣት ያቃተው መሆኑ በግልፅ አሳይቶናል፡፡
በኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ በየሀገሩ የሚደርሰው ሰቆቃ አዲስ ባይሆንም በቅርብ ግዜ ወዲህ በማዕከላዊ ታንዛኒያ በጫካ ውስጥ ተጥለው የተገኙ ኢትዮጵያውያን ጉዳይ እጅግ በጣም አሳዛኝና አስደንጋጭ ነው፡፡ እነዚህ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ከሀገራቸው ከወጡ በኋላ በማላዊ አቆራርጠው ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመግባት ሲሉ በኮንቴይነር ተጭነው በታንዛኒያ በኩል ሲጓዙ አየር አጥተው በመታፈናቸው 43ቱ ሕይወታቸው ሲያልፍ በርካቶቹ ለጉዳት ተዳርገዋል፡፡ ይህ ድርጊት የወያኔ/ህውሃት  መንግሥት በካድሬያዊ የአፈና አገዛዙ ከቀዬአቸው እያፈናቀለ በሰው ሀገር ለስቃይ የሚዳርጋቸው ዜጎች ስፍር ቁጥር የሌለው መሆኑን ማሳያ ነው፡፡
ወያኔ/ህውሃት ይህ አልበቃ ብሎት በሞኖፖል በሚቆጣጠረው ኢቲቪ በሟቾች ቀብር ስነሰርዓት አስታኮ በሀገሪቱ ስለአለው ልማት፣ ልማቱን ተከትሎ ስለአለው ፍሰሃና ደስታ ፕሮፓጋንዳ በመንዛት ዜጎችን ለስደት የሚያበቃቸውን ዋናኛ መንስዔ ለመደበቅ ሲዋትት፤በተጎጂዎችም ላይ ሲያላግጥ ማየት አሳፈሪ ክስተት ሆኖ አግኝቸዋለው፡፡
ስደት ድህነት ነው ድህነት የብልሹ ፖለቲካ ስርዓት ውጤት ነው
በሳውዲ ውስጥ ሆኜ ስቃይ፣ግፍ፣ግድያ፣ደብደባ እያየ የሚዳክረው ወገኔ ሳውዲ ዋና ከተማ ሆኜ ስንቱን ጉድ አየሁ አለ ወገኔ፡፡ ስንቱ ስደተኛ ላይ የደረሰውን እያየሁ አለቀስኩ፡፡ ኡኡኡ….ድረሱ አልኩ፡፡ኢትዮጵያን እንወዳለን የምትሉ ሰዎች ህዝቡን ሳይሆን ባዶ መሬቱን ድንጋይ አፈሩን ነው እንዴ የምትወዱት ወገን አለቀ ድረሱ…ብያለሁ፡፡ከሳውዲ የወገኖቻችን ጩኸት ነው!።
እውነት ለህዝብ ተቆርቋሪ መስሎ ለመታየት ካልሆነ በስተቀር ከዚህ በፊት ኧረ!…የወገን ያለህ ይህን ያህል ዜጋ አለቀ ስንል ምነው ምላሽ የሚሰጠን ጠፋ? አንድ በሉ፡፡ ይህን ያህል ዜጋ ታፍኗል፣ 14 ሺህ ኢትዮጵያዊያን ሀረጥ የሚባለው ካምፕ ውስጥ ታጉረው ወደሀገር የሚመልሰን ጠፋ ሀገራችን መልሱን ብለው ሰላማዊ ሰልፍ እስኪወጡ ድረስ በርሃብ ሲቆሉ…ሲረግፉ መልስ መቼ ሰጡ? ሁለት በሉ፡፡ በስንት ሺህዎች በየጎዳናው እስኪረግፉ ቀባሪ አጥተው በየመንገዱ ወደቁ ኧረ የሰሚህ ያለህ ስንል ዝምታው ለምን ነበር?
አሁንም ይሄ ሁሉ አታሞ ድሰቃ እውነት ለስደተኛው ሊሰራ ታስቦ ከሆነ አልረፈደም፡፡ ግን ከልብ አለመለቀሱ እነሱ ውይይት ብለው በተቀመጡበት ቀን እዚህ የመን ውስጥ ስንቶች በአፋኞች መከራቸውን እየበሉ ነው? ስንቶች ተደብድበው አካላቸውን አጥተዋል? እውነት ድንበሩ ከተዘጋ በዚህ ሳምንት ብቻ ወደ የመን የተሻገረው ህዝብ ብዛት በሺህዎች መሆኑ እና የIOM (ዓለም አቀፍ የስደተኞች ድርጅት) ሰራተኞች ከቁጥጥራቸው ውጭ መሆኑን ማሳወቃቸው ምን ያሳያል፡፡ ዛሬም እየተዋሸ ፖለቲካዊ ድስኮራ መሆኑን አያሳይም? ተሰብስቦ ከማውራት ወደ ተግባር መሸጋገር ነው የሚያስፈልገው፡፡
ስለቻይና እድገት ባልተያያዘ መልኩ የከተማልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስትሩ ብዙ አወሩ፡፡ ባለ ሁለት ዲጂት ተከታታይ እድገት አስመዘገበች በተባለው ኢትዮጵያ ድህነት የለም ለማለት ሞከሩ፡፡ በድህነት አይደለም የሚሰደዱት አሉንም፡፡ እግዚአብሄር ይስጣቸው አንባሳደር ዲና ሙፍቲ ለሆዳቸው ብለው የአይጥ ምስክር…ያስባሉንን እውነቱን ነገሯቸው፡፡ ሁለቱን ነጣጥለን አንመልከት ድህነት አይደለም ያሰደዳቸው ማለት ስህተት ነው አሉም፡፡ የውይይት አቅጣጫውን ግንዛቤ በማነስ ስደት እንደሚወጣ ለማድረግ የሞከሩ ሰዎች በዝተው መታየታቸውና እንዲያውም በጉዳዩ ላይ ጥናት ያደረጉ መሆናቸው መናገራቸው ደግሞ ድራማውን አስቂኝ ያደርገዋል፡፡ ጥናት ቢያደርጉ እውነት ይሄን ነበር የሚናገሩት? ማህበራዊ ድረ-ገጾችን ቢያገላብጡ የውጭ መገናኛ ብዙሀንን ቢከታተሉ እንኳን ችግሩ ገብቷቸው ይናገሩ ነበር፡፡ ግን ባልሰሩት፣ ባላዩት ጥናት አቅራቢ ሆነው ለተከራከሩት ሰዎች አንድ እውነት አስረግጬ ልነግራቸው ወደድኩ፡፡
ግንዛቤ ማጣትም ሆነ ገንዘብ ማጣት ሁለቱም ደህነት ነው፡፡ ስደት በየትም አልነው በየትም አሽሞነሞነው ስደት ድህነት ነው፡፡ ድህነት ደግሞ የብልሹ ፖለቲካ ስርዓት ውጤት ነው፡፡ ሰላም አጥቶ መብቱ ተረግጦ የሚሰደደው ኪሱ የዳለበውም ቢሆን የሰላም ደሀ ሆኖ ነው፡፡ ሌላ ታፔላ መለጠፉም ሆነ ማሽሞንሞኑ ስደትን አያጠቁረውም አያቀላውም፡፡ ጥናት አጥንተናል ባዮችም ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ እንዲሉ ነውና ይልቅ የመፍትሄ ሀሳብ አቅርቡ…ህገ-ወጥ ደላሎች ያላቸውን ተዋረድ እና ሰንሰለት መናገሩ ብቻ ምን ፋይዳ አለው፡፡ እዚህ የመን፣ሳውዲ ያለ ኤምባሲ ስንት የሚያዙትን ህገ-ወጥ ደላሎች ሲፈቱ ዝም ከማለት ውጭ ምን አደረገ? አሁን በቅርቡ ያየነው እንኳን ስልሳ ኢትዮጵያዊያንን አፍኖ የተያዘ ሰው ሲፈታ ዝም አይደል ያሉት ያውም ከነደበደባቸው 60 ልጆች ተይዞ እሱ ወጥቶ ልጆቹ ታስረው ቀርተዋል፡፡ አሁንስ ቢሆን በየመን ህገ-ወጥ አጓጓዦች ከኤምባሲው ምን ደረሰባቸው ገብተው ይወጣሉ፡፡ እጅና ጓንት ናቸው፡፡ የመንግስት ስራ ሁሉ የይምሰል ነው፡፡
ማፈሪያ የሆነው ETV ህገወጥ የሰዎች ዝውውር በሚል ዶክመንተሪ የሚመስል ነገር አሳይቶናል፤በጣም የሚያሳዝን ነው።ስለ ወገንም የማያዝን ልብ የለንም።ነገርግን ይህ ስርሃት አልበኛ መንግስት ያወጣው ወገንን የመፍጀት ስትራቴጂ አንዱ አካል ይመስለኛል፤ለወገን ተቆርቋሪም ሆኖ አይደለም ይህንን ዶክመንተሪ ያሳየን።
ወገኖቻችን ለምንድነው ለዚህ አደጋ ራሳቸውን የሚያጋልጡት?
ጉዳት የሚያደርስ መሆኑን እያወቁ ለምን ይህን አደጋ ይጋፈጣሉ?አማራጭ ማጣት ነው።
ህዝቡ ተስፋ እንደቆረጠ ያሳያል፤እንጂ ወያኔዎች እንዳሰቡት ምንም ትርፍ አያመጣም።
ምነው በየአረብ አገራቱ ከደረሱ በኋላ እንኳን ቆንስላ ፅ/ቤት ሄደው አቤቱታቸውን እያሰሙ ለ3ናለ4 ቀናት በየቆንስላው በር ላይ ተቀምጠው የሲሚንቶ ቅዝቃዜና ውርጭ ሲፈራረቅባቸው እያዩ አላየንም ነበር ሊሉን አስበው ይሆን?
ታዲያ አሁን አዝነናል ለማለት በምን ሞራል ነው የሚነፋረቁት?
እውነታው ግን የኛ መንግስት ሁሉ ነገር ለፓለቲካ ጥቅም እንጂ ለሀገር:ለህዝብ ተብሎ የሚሰራው ነገር የለም ማለት ነው ?
እስከ ዛሬ ድረስ ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች ወዳጅ ዘመዶች መጽናናትን እመኛለሁ፡፡ ለችግሩ ዘላቂ መፍትሔ የሚሆነው የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ እውን እስኪሆን ድረስም ትግሉን የኢትዮጵያ ህዝቡ  አጠናክሮ መቀጠል አለበት ፡፡
ከሁሉም በላይ ለዜጎች መፈናቀል፣ ፍልሰትና ስደት መንስኤ የሆኑ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ችግሮች እንዲወገዱ  የወያኔ/ህውሃት  የሕግ የበላይነትን ለማክበርና ለማስከበር እንዲሁም መልካም አስተዳደርንና ፍትሕን ለማረጋገጥ የሚያስችል እርምጃ በአፋጣኝ እንደማይወስድ ተረድተን እኛ መፍትዬ ልናበጅ ይገባል።
በመጨረሻም ሕዝባችን  ለዜጎች ሰብአዊና ደሞክራሲያዊ መብቶች መከበር ትኩረት ሰጥቶ እንዲንቀሳቀስና የሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነትን እንዲያረጋግጥ አስፈላጊውን ጫና እንዲያደርግ ጥሪዬን አሰተላልፋለው፡፡
http://ecadforum.com/Amharic/archives/10196/

http://ethiolion.com/Pdf/11192013teteyakiwe_woyane_newe.pdf

http://ethiomedia.com/13report/teteyaqeew_weyane_naw.pdf

http://www.ethiomunchen.de/

http://articles2u.files.wordpress.com/2013/11/article1.pdf   or http://www.debteraw.com/

http://assimba.org/Articles/LeZegoch_Sidet_Teteyakiw_Woyane_New.pdf

http://www.maledatimes.com/?p=9675

No comments:

Post a Comment