Saturday, May 23, 2015

ዞን9 ጦማርያን በብሎገርነት ሽፋን ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር አንደሚሰሩ እርግጠኞች ነን ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም በአልጀዚራ ቴሌቭዥን


ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ምርጫውን አስመልክቶ ከአልጀዚራ ቴሌቭዥን ጋር ቆይታ ባደረጉበት ወቅት በተደጋጋሚ ስለዞን9 ጦማርያን አና ሶስቱ ጋዜጠኞች ተጠይቀው በጥቅሉ የሚከተሉትን ምላሾች ሰጥተዋል፡፡

1. ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር አንደሚሰሩ እርግጠኞች ነን ብሎገርነት ስም ሽፋን ነው
 ፡፡

2. ፓርላማ በሽብር ከመደባቸው ድርጅቶች ጋር እንደሚሰሩ ማስረጃ አለኝ የድርጅቱን ስም ግን አሁን አልናገርም ምክንያቱም የፍትህ ሂደቱ ላይ ተጽእኖ ላመጣ እችላለሁ
 ፡፡

3. ከሽብርተኛ ድርጅት ጋር ላለመስራታቸው (ለፍርድ ቤቱ) ማስረዳት አለባቸው
 ፡፡

4. አንድ ዓመት እስር ለሽብር ህግ ምንም ማለት አይደለም
 ፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር አስመልክቶ ከዚህ በፊት በእስር ላይ ከሚገኙት ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ግልጽ ደብዳቤ የጻፍን ቢሆንም ጠቅላይ ሚንስትሩ በዛሬውን ንግግራቸው የተለመደውን የአመክንዮ፣ የሃቅ እና የህግ ስህተቶች ፈጽመዋል ፡፡

1. የዞን9 ጦማርያን የሽብርተኛ ድርጅት አባል ለመሆናቸው የቀረበባቸው ምንም የአባልነት ማስረጃ የለም ፡፡ ፍርድ ቤት ላይ የቀረቡ ማስረጃዎችም ይህንን አያስረዱም ፡፡

2. በፍርድ ቤት የተከሰስነው የግንቦት ሰባት እና የኦነግ አባልነት መሆኑ በግልጽ ተቀምጦ ሳለ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሚስጥር ማስመሰላቸው ጉዳዩ ላይ እውቀት አንደሌላቸው ያስረዳል፡፡


3. በመሰረታዊ የህግ መርሆ መሰረት ከሽብርተኛ ድርጅት ጋር አለመስራታችንን ማስረዳት ሳይሆን መንግስት በአቃቤህግ በኩል ወንጀል መስራታችንን ነው ማስረዳት ያለበት ፡፡ የማስረዳት ሸክሙን እኛ ላይ በመጣል መሰረታዊ የህግ ጥሰት ከመፈጸማቸውም ውጪ መንግሰታቸው የሚሰራበትን “ሁሉም ሰው ወንጀለኛ ነው ወንጀለኛ አለመሆኑን ማስረዳት አለበት” የሚል ትችት የሚሰነዝሩ ዜጎችን አንደወንጀለኛ የማየት አቅጣጫ ፍንትው አድርጎ ያሳያል ፡፡ በዚህም ወጣት የህግ ባለሞያዎች እንዳሉበት ስብስብ አፍረናል፡፡


4. መሰረታዊ የሆነው አፋጣኝ ፍትህ የማግኘት መብት በተራዘመ ምርመራ እና የፍርድ ቤት ቀጠሮ መጉላላት መጣሱ መንግስትን አንደማያሳስበው ማየታችን አሁንም አሳፍሮናል፡፡ አገራችን በፈረመቻቸው አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ህጎች መሰረት አፋጣኝ ፍትህ ማግኘት የዜጎች መብት ሲሆን የመንግሰት ከፍተና አመራረር ያለምንም ማፈር የመብት ጥሰቱን መከላከላቸው አስገራሚ ነው ፡፡


በመሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆነ ሌሎች ከፍተኛ የመንግሰት ባለስልጣናት ያልተፈረደባቸውን ተከሳሾች ሽብርተኛ በማለት መፈረጃቸው አንዲያቆሙ ፣ መሰረታዊ የወንጀል ህጎቸን አንዲያከብሩና አንዲያስከብሩ ልናሳስብ አንወዳለን፡፡
የዞን9 ጦማርያንም ሆነ ወዳጅ ጋዜጠኞች በምንም አይነት ወንጀል ተሳትፈው የማያውቁ ሲሆን ክሳቸውም ፓለቲካዊ ነው ፡፡ ተከሳሾቹን በነጻ ማሰናበት ለመንግሰት በጣም ቀላሉ ችግሩን የመፍቻ መንገድ ነው ፡፡


ስለሚያገባን እንጦምራለን!

ዞን 9


http://www.zehabesha.com/amharic/archives/41602

No comments:

Post a Comment