Thursday, January 31, 2013


ውሃም በፈረቃ ``ኢትዮጵያ ጂቡቲን ንፁህ ውኃ ልታጠጣ ነው``

በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎች የውሃ እጥረቶች እየገጠማቸው መሆኑን ገለጹ። ነዋሪዎች በአካባቢዎቹ የተከሰተው የውሃ እጥረት በእለት ተእለት ህይወታቸው ላይ ተጽእኖ እየፈጠረባቸውን እንደሚገኝ ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ አገልገሎት በበኩሉ በአዲስ አበባ በአንዳንድ አካባቢዎች ችግሩ መኖሩንና ለዚህም ውሃን በፈረቃ እያዳረሰ መሆኑን አስታውቋል። በሳምንት ሶስትና ሁለት ሲበዛም አንደ ጊዜ ብቻ ውሃ የሚያገኙ አካባቢዎች እንዳሉም ነው የመስሪያ ቤቱ ምክትል ስራ አስኪያጅ የተናገሩት።

ከኢትዮጵያ የድንበር ከተማ አንስቶ 70 ኪሎ ሜትር በሚዘረጋ የውኃ ማስተላለፊያ መስመር ኢትዮጵያ ጂቡቲን ንፁህ ውኃ ልታጠጣ ነው፡፡

በገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትሩ አቶ ሱፊያን አህመድ የሚመራ የልዑካን ቡድን ባለፈው ሳምንት ይህንን ፕሮጀክት በሚመለከት ከጂቡቲ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር ከመከረ በኋላ ይሁንታውን ሰጥቷል፡፡ የጂቡቲ መንግሥት ግንባታውን በ18 ወራት ውስጥ ለማጠናቀቅ ዕቅድ አውጥቷል፡፡

የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር የሕግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ዋሲሁን አባተ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የግንባታው ወጪ በጂቡቲ መንግሥት ይሸፈናል፡፡

ኢትዮጵያ ለጂቡቲ ከምትሰጠው የመጠጥ ውኃ ኪራይ እንደማታስከፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ጂቡቲ ግን ከድንበር እስከ ጂቡቲ ከተማ ለሚዘረጋው የውኃ መስመር የሚወጣውን ወጪ ትሸፍናለች፡፡ ሀዳጋላ የሚባለው አካባቢ የሚገነባው የውኃ ማመንጫ ጣቢያ አንድ መቶ ሺሕ ሜትር ኪዩብ ውኃ የማመንጨት አቅም አለው፡፡

ኢትዮጵያ ለጂቡቲ ውኃ ብቻ አይደለም የሰጠቻት፡፡ ከዚህ ቀደም በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ አርሲ ዞን ውስጥ ሴሮፈታ አካባቢ ስንዴ የሚመረትበት ሦስት ሺሕ ሔክታር መሬት ሰጥታለች፡፡

ይህ መሬት ቀደም ሲል በፕራይቬታይዜሽንና በመንግሥት የልማት ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ ሥር በሚገኘው የባሌ እርሻ ልማት ድርጅት ይተዳደር ነበር፡፡ መንግሥት ይህንን መሬት በቀጥተኛ ውሳኔ ለጂቡቲ መንግሥት እንዲተላለፍ አድርጓል፡፡ ለስንዴ ምርት ምቹ የሆነው ይህ መሬት ከ60 ሺሕ ኩንታል በላይ ስንዴ እንደሚመረትበት ታውቋል፡፡

‹‹ሴሮፈታ ሞደርን ፋርም ኦፍ ዘ ሪፐብሊክ ኦፍ ጂቡቲ›› በሚል ስያሜ የሚታወቀው ይህ እርሻ፣ በየዓመቱ 2,828 ሔክታር መሬት ታርሶ ስንዴ ይመረትበታል፡፡

ትንሿ የአፍሪካ ቀንድ አገር የሆነችው ጂቡቲ ጠቅላላ ስፋቷ 23,180 ካሬ ኪሎ ሜትር ነው፡፡ ጂቡቲ ለኢትዮጵያ ዋነኛ ወደብ አቅራቢ መሆኗም ይታወቃል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ከኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል በማግኘት ቀዳሚዋ አገር ሆናለች፡፡
    
    Posted By.Dawit Demelash

No comments:

Post a Comment